Thursday, July 24, 2014

ወይንሸት ፍርድ ቤት ቀረበች፣ አቤል ኤፍሬም ታሰረ፣ የሰማያዊ ፓርቲ ወጣቶችን ማሰሩ እና ማዋከቡ ቀጥሏል

ኢየሩሳሌም ተስፋው (አዲስ አበባ)

ዛሬ የወይኒ ፍ/ቤት ቀጠሮ ስለሆነ በጠዋት የሰማያዊ ልጆች ከያለንበት ተሰባስበን ሜክሲኮ ወደሚገኘው እንደኛ ደረጃ ፍ/ቤት ሄድን ተሰባስበን ግቢ ውስጥ ቀመን ሳለ እነወይኒን የያዘው መኪና ሲመጣ ባለፈው ያየነውን ሽብር መንዛት ጀመሩ መብታችን አይደል እንዴ መከታተል እንዴት ከግቢ ታስወጡናላችሁ? አልን ከመሃላችን አቤል ኤፍሬምን ና ብለው ወደ ውስጥ አስገቡት እንዴ ለምን ትወስዱታላችሁ ስንል ቆይ አናግሬያቸው መጣሁ ብሎን ገባ የነወይኒ መኪናም ውደውስጥ ገብቶ መውረድ ጀመሩ ወይኒዬ ጭንቅላቷ እና እጇ እንደታሸገ ነው ፊቷ ላይ እሚነበበው ጥንካሬ አሁንም እንዳለ ቢሆንም አካሏ ግን እንደተጎዳ በደንብ ያስታውቃል ከፍተኛ ድብደባ እየደረሰባት እንደሆነ ትናንት ለነ ጌች ነግራቸዋለች እጥፍጥፍ ብላ አንገቷን ደፍታ ስትቀመጥ ሳያት የእውነት ከዚች አገር መፈጠራችንን ነው የጠላሁት ወይኒ እያየችን ከቁጥጥሯ ውጭ በሆነ መልኩ እንባዋ ይፈስ ጀመር ጭንቅላቷን እና እጇን እየነካች የስቃይ ፊት አሳየችኝ እሱንም ፖሊሶቹ እንዳይዋት በመሳቀቅ ነው በዚህ ሁሉ ስቃይ መሃል እጇን እየሳመች እንደምትወደን ደጋግማ ታሳየናለች።

ችሎት ገቡ ለሐምሌ 24 እንደተቀጠረ ከዛሬ ጀምሮ ሰው እንዲጠይቀት ፍ/ቤቱ እንዳዘዘ ነገረችን የነሱ መኪና ሲወጣ ወደ ቀጣዩ እስረኛ ጓዳችን ተጠግተን ለመጠየቅ ስንሞክር ሁከት ለመፍጠር ሙከራ አድርጓል ስለዚህ ሶስተኛ ወስደንዋል እዛ ሂዱና ጠይቁ አለን አንድ ጥጋብ አናቱ ላይ የወጣ ፖሊስ እኮ ወንጀሉ ምንድነው? ሁከት መፍጠር ምንም አይነት ሁከት አልፈጠረም መብቱን ነው የጠየቀው ያ ደግሞ ወንጀል ከሆነ ሁላችንም ወንጀለኞች ነን ሁላችንንም እሰሩን አቤል ምንም አይነት ወንጀል አልሰራም ብለን ሊቀ መንበራችን ኢ/ር ይልቃልን ጨምሮ ወደ 30 እምንሆን የሰማያዊ ልጆች ተሰብስበን ገባን።


ከዛ በኋላ ምን ብዬ ልንገራችሁ ሁሉም እየተነሳ አፉን ይከፍትብን ጀምር እደፋሃለው እገልሃለው ተው አታስፈራራኝ ይለዋል ፍቅረማርያም ማስፈራራት ነው የገረመህ በድርጊት አሳይሃለው አለው ብርሃኑን ደግሞ ከዚህ በፊት እዛ ታስሮ ሳለ እሚያውቀው አንድ ፖሊስ እንተ ቤቱን ታውቀዋለህ አይደል አሁንም አስገባሃለው አለው በጣም የሚገርመው እንዲህ የሚደነፉት እኮ ተራ ፖሊሶች ናቸው።

ምንም አይነት ጥፋት የለብንም መብታችንን ነው የጠየቅነው ስንል መብታችሁን እዚህ አይደለም እምጠይቁት አለን ቆይ ፍ/ቤት መብታችንን ያልጠየቅን የት ነው እምንጠይቀው ታድያ? ሁልሽም እዛ ወስደን ስንቀጠቅጥሸ ጥጋብሽ ይወጣልሻል አለ ተሰብስበን ተቀመጥን እነሱም ይደነፋሉ ይህ ስርዓት ምን አይነት ደረጃ ላይ እንደደርሰ እና የራሱን እድሜ በራሱ አያሳጠረ መሆኑን እያሰብኩ በእልህ ስሜት ተቀምጠናል በተደጋጋሚ ያስፈራሩናል እንድንወጣ ካለበለዚያ እሚመጣው ነገር አስፈሪ መሆኑን ይነግሩናል በቃ እሚመጣውን ነገር ለመቀበል ዝግጁ ነን ውሰዱን አታስፈራሩን በቃ አልን፣ ይልቃልን ጠሩት እና ያዋሩት ጀመር ይህ ፍ/ ቤት መሆኑን መቀመጥ እንደማንችል ሰዓት ስለደረሰ የፍ/ቤቱ ግቢ ሊዘጋ መሆኑን እና በሰላም እንድንወጣ ይህ ህገወጥ ድርጊት መሆኑን ብቻ ብዙ ነገር ለፈለፉ ስለአቤል ጉዳይ ሔደን እዛ እንድንጠይቅ ነግረውት መጣ እኛም ወጣን አቤሎን ይዘውት ሄዱ አዎ ተራ በተራ እየለቀሙ ያስገቡናል የሁላችንም ቤት እዛው ነው የጊዜ ጉዳይ ነው።

“በሉ እናንተም ሂዱ የኛም ወደዛው ነው ወትሮም መንገደኛ ፊት እና ኋላ ነው” ቀጣይ ተረኛ ደግሞ ማን ይሆን? ላንቺ ነው አገሬ ላንቺ ነው
ላንቺ ነው ኢትዮጵያ ላንቺ ነው

አዎ ይህ ሁሉ ስቃይ እየደረሰባቸው ያለው አንቺን በማለታቸው ብቻ ነው!

No comments:

Post a Comment