ድምፃችን ይሰማ!

እንግዲህ በህገ መንግስቱ መግቢያና በአንቀፆቹ የተገለፁትን ሃሳቦች ጠቅለል ባለ መልኩ ከተመለከትናቸው በሃገራችን የሚመሰረተው መንግስት ህዝብን ለማገልገል የሚመሰረት ተቋም መሆኑን እና የመንግስት አካል ሆነው የሚፈጠሩ ማናቸውም ክፍሎች ለህገ መንግስቱ ተገዢዎች፣ እንዲሁም ህገ መንግስቱን በተግባር ለመተርጎም የሚፈጠሩ መሆን እንዳለባቸው እንረዳለን፡፡ በተቃራኒው ህገ መንግስቱን የማፋለስ እና የመርገጥ መብት የሌላቸው መሆኑንም እንገነዘባለን፡፡ በተጨማሪም በማንኛውም የመንግስት ተቋማት ተቀጥሮ የሚሰራ ግለሰብ ዋነኛ እና ከፍተኛ ኃላፊነቱ ህዝብን ማገልገል እና የህዝቡን ጥቅም እና ነፃነት መጠበቅ መሆኑን እንረዳለን፡፡
ከዚህ መሰረታዊ ሃሳብ ከተነሳን በመንግስት ተቋማት ውስጥ በመቀጠር የህዝብን መብት እና ነፃነት የሚጋፉ፣ ወይም የማህበረሰባቸውን መብት እና ነፃነት የሚገፍ ማንኛውንም ትዕዛዝ የሚቀበሉ፣ የሚፈፅሙ እና የሚያስፈፅሙ አካላት ቢያንስ የሚከተሉትን ሶስት መሰረታዊ የህገ መንግስት ጥሰቶች መፈፀማቸውን ልንገነዘብ እንችላለን፡-
1. አንድ ግለሰብ በሃገራችን ሉዓላዊው አካል እና ከፍተኛ የስልጣን ባለቤት ህዝብ መሆኑን እያወቀ የህዝብን ደህንነት እና ነፃነት የሚጋፉ ድርጊቶችን እንዲፈፅም የሚሰጠውን ትዕዛዝ መቀበሉ እሱም የህዝቡ አካል ነውና በቅድሚያ የራሱ ህገ መንግስታዊ መብት እንዲረገጥ በፍቃደኝነት የተቀበለና ለህገ መንግስቱ ክብር የሌለው መሆኑን ያረጋግጣል፤
2. ግለሰቡ የህብረተሰቡን መብት የሚጥሱና ነፃነቱን የሚያቃውሱ ድርጊቶችን እንዲፈፅም ታዝዞ ድርጊቱን ከፈፀመ የወገኖቹን የህገ መንግስት መብት የሚጥስ እና የሚረግጥ በመሆኑ ዳግም ህገ መንግስቱን ይጥሳል፤ ይረግጣል፤
3. ህገ መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል በማለት ተቃውሞ የሚያሰሙ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለማፈን እና ይህን መብታቸውንም ለመግፈፍ የተሰማራ ከሆነ በሶስተኛ ደረጃ ህገ መንግስቱን ይጥሳል፤
በመሆኑም እያንዳንዱ ዜጋ በሚያደርገው ድርጊት ዛሬ መንግስትን በታማኝነት ሲያገለግል ድርጊቱ ከህገ መንግስቱ ጋር የሚጣጣም እና የህገ መንግስቱን መንፈስ የተከተለ መሆን አለመሆኑን የማጣራት ግዳጅ ያለበት ሲሆን ይህንን ችላ ብሎ ህገ መንግስቱን የሚፃረሩ ድርጊቶችን መፈፀሙ ነገ የህግ የበላይነት በሃገሪቱ ሲሰፍር እና እኛ የኢትዮጵያ ህዝቦች መብታችንን በፍትሃዊ ፍርድ ቤት የምናከብርበት ወቅት ሲመጣ በህገ መንግስቱ መሰረት ለፍርድ የሚቀርብ መሆኑን ሊገነዘብ ይገባዋል፡፡ ይህን ከግምት በመክተት እያንዳንዱ ዜጋ ህገ መንግስቱን ተገንዝቦ የራሱን መብት አክብሮ የሌላውን ወገኑን መብት እንዲያከብር አጥብቀን በወገናዊነት ስሜት እንጠይቃለን፡፡ ታማኝነት ለህግ እና ለህገ መንግስቱ እንጂ ራሳቸውን ‹‹የህዝብ ተወካዮች›› ሲሉ ሰይመው ህዝብን ለመርገጥና መብት ለመግፈፍ ለቆሙ ጥቂት አምባገነኖች አይደለም! የአምባገነኖች አገልጋይና መሳሪያ በመሆን ካገለገሉ በኋላ ‹‹ህዝብ ላይ በደል የፈጸምኩት በእነሱ ትዕዛዝ ነው›› ማለት ከተጠያቂነት አያድንም!
ህገ መንግስቱን ማክበር እና ማስከበር ህዝባዊ ሀላፊነታችን ነው!!!
ትግላችን እስከድል ደጃፎች በአላህ ፈቃድ ይቀጥላል!
No comments:
Post a Comment