Saturday, January 31, 2015

የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ኢትዮጵያ ውስጥ ኖሮ አያውቅም

የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ኢትዮጵያ ውስጥ ኖሮ አያውቅም

(ecadforum.com ኢዲቶሪያል)

ሰሞኑን ወያኔ/ኢህአዴግ በህግ ተመዝግበው በሀገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የተቃዋሚ ፖለቲካ ድርጅቶችን ለማጥፋትና በመጪው ምርጫ ላይ እንዳይሳተፉ ለማድረግ በርትቶ እየሰራ መሆኑ ይታወቃል።


እስካሁን መኢሕአድ እና አንድነት ፓርቲ የዚሁ የወያኔ/ኢሕአዴግ የቅድመ ምርጫ “ተቃዋሚዎችን የማዳከም እና የማጥፋት ዘመቻ” ሰለባ ሆነዋል።


በቅርቡ ራድዮ ፋና እና ኢቲቪ ከሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ጋር አድርገውት የነበረውን ቃለ-ምልልስ (በኋላ የቃለ-ምልልሱ ድምጽ ጠፋብን ማለታቸው ይታወሳል፣ ይሁንና ኢሳት ቴሌቪዥን ጠፋ የተባለው ቃለ-ምልልስ በእጁ ገብቶ ኖሮ እያሰራጨው ይገኛል) ቃለ-ምልልሱን ለማዳመጥ እዚህ ይጫኑ። ከቃለ-ምልልሱ መረዳት እንደሚቻለው ፖሊስ ቀመሱ የወያኔ/ኢሕአዴግ ጋዜጠኛ ምን ያህል ሰማያዊ ፓርቲን የሚያስወነጅሉ ነገሮች ፍለጋ ይባዝን እንደነበር ነው። ይህ የሚያመለክተው ሰማያዊ ፓርቲ ቀጣዩ የወያኔ/ኢህአዴግ “ተቃዋሚዎችን የማዳከም እና የማጥፋት ዘመቻ” ሰለባ እንደሚሆን ነው።

ወደ ተነሳንበት ርዕስ ስንመለስ፣ ከላይ የተጠቀሱትን ሁነቶች ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ አንዳንድ በተቃውሞ ጎራ የተሰለፉ ፖለቲከኞች እና ለውጥ አራማጆች “ወያኔ/ኢሕአዴግ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓትን እያቀጨጨ ነው፣ ገዢው ፓርቲ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓትን እያጠፋ ነው፣ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት አከተመለት…” ሲሉ ይደመጣሉ።


ለመሆኑ ኢትዮጵያ ውስጥ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ኖሮ ያውቃል? አይደለም የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ሊኖርና ወያኔ/ኢህአዴግ ወደፊትም የመድበለ ፓርቲ ሥርዓትን ለመገንባት ፍላጎት የለውም።

ምርጫ በተቃረበ ቁጥር ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞችና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ይታሰራሉ፣ ይደበደባሉ፣ ይዋከባሉ፣ ሲከፋም ይገደላሉ። የፖለቲካ ድርጅቶችም ይፈርሳሉ፣ በተለጣፊም ይቀየራሉ። እውነታው ይህ ነው፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ኖሮም አያውቅም።

ይልቁኑ ወያኔ/ኢሕአዴግ “ኢትዮጵያ ውስጥ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት አለ” ብሎ ማሳመን ችሎ ኖሯል።

በመድበለ ፓርቲ ሥርዓት የበለጸጉት ምዕራባውያን የወያኔ/ኢሕአዴግ ግብረ-አበሮችም የሚፈልጉት ነገር ቢኖር ወያኔ/ኢሕአዴግ በተቻለው መጠን የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት አንዳለ እንዲያስመስልና ይህንኑ እንዲደሰኩር እንጂ ኢትዮጵያ ውስጥ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት እንደሌለና ወያኔ/ኢሕአዴግ ወደፊትም የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ለመገንባት ዝግጁ እንዳልሆነ በሚገባ ያውቃሉ።

ኢትዮጵያ በአምባገነን ሥርዓት ቁጥጥር ስር የምትገኝ ሀገር ናት፣ ዜጎቿም በአምባገነኖች ተረግጠው እየተገዙ ነው። ማንኛውም ለውጥ አራማጅና ለውጥ ፈላጊ በቅድሚያ ከዚህ እውነታ ጋር መታረቅ ይሆርበታል/ይኖርባታል። ይህ ሲሆን ብቻ ነው በምን አይነት መንገድ ታግሎ የወያኔ/ኢሕአዴግን የአምባገነን ሥርዓት ማስወገድ እንደሚቻል መቀመር የሚቻለው።

No comments:

Post a Comment