Sunday, April 27, 2014

“እኛም ከሚሊዮኖቹ ውስጥ ነን”

የኢትዮጵያ ሕዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ (ሸንጎ)
Ethiopian People's Congress for United Struggle (Shengo) www.ethioshengo.org shengo.derbiaber@gmail.com

“እኛም ከሚሊዮኖቹ ውስጥ ነን”

  ሚያዝያ 19፣ 2006
 (ኤፕሪል 27፣ 2014)

የኢትዮጵያ ሕዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ (ሸንጎ)፣ በአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) እየተቀነባበረ በሚካሄደው “የሚሊዮኞች ድምፅ” ንቅናቄ ውስጥ “እኛም ከሚሊዮኞቹ ውስጥ ነን” በማለት ለተጀመረው እንቅስቃሴ ሙሉ ድጋፉን እንደሚሰጥ ሲገልጽ በታላቅ ደስታ ነው። በዚህም መሠረት የዚህ እንቅስቃሴ አካልነታችንን በተግባር ለመግለፅ በአዳማ (ናዝሬት) የሚካሄደውን እንቅስቃሴ በስፖንሰርነት ለመደገፍ እድሉ ስለገጠመን እጅግ ደስተኛ ነን።

ሸንጎ በተደጋጋሚ እንደገለጸው፣ በሀገራችን ውስጥ የሰፈነው የግፍ፣ የአድልዖና የከፋፋይነት ሥርዓት ማብቃት አለበት። ሥርዓቱ የሀገሪቱን ሕዝብና ሁሉንም የሀገሪቱን አካባቢ በከፍተኛ አደጋ ላይ ጥሏል። ኢትዮጵያን የባሕር በር የሌላት ከማድረግ ጀምሮ ዜጎቿን እርስ በርስ በጥርጣሬ እንዲተያዩ አልፎም እያንዳንዱ ዜጋ ያለፍትኅ እየተጎተተ የሚታሠርበት፣ የሚደበደብበት፣ ከሥራና ከንብረቱ የሚፈናቀልበት ሀገር እስከመሆን ደርሰናል። ገዥው ቡድንና ሥርዓቱ የሚመራበት ፖሊሲና ተግባሩ እንኳንስ ለአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ቀርቶ፣ ለራሱ ለሥርዓቱ ደጋፊዎች የማይበጅ ኢንደሆነ ሁሉም የሚገነዘበው ነው።


ይህ አስከፊ ሁኔታ እንዲያከትምና በሕጋዊና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲተካ ለማድረግ ደግሞ በአንድ በኩል የተቃዋሚ ድርጅቶች ተሰባስበው የተቀነባበረ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ማካሄድ ሲገባቸው በሌላ በኩል ደግሞ ኢትዮጵያውያን ሁሉ የተጀመሩትን አበረታች እንቅስቃሴዎችን በተግባር እንዲያጠናክሩ ይጠበቃል። በዚህ መልክ ስንሰባስብና ሃላፊነት በመውሰድ ትግሉን ስናጠናክር የወገኖቻችን ስቃይና በሀገራችን ላይ የተጋረጠው አደጋ ማብቂያና የብሩኅ ተስፋ ዘመን መጀመሪያ ጊዜ እጅግ የቀረበ ይሆናል።

ለዚህ ነው ሸንጎው በኢትዮጵያ ሀገራችን አንድነት የሚያምኑትን የተቃዋሚ ኃይሎች በጋራ እንድንሰባሰብ ደግሞ ደጋግሞ የሚጠራው። ለዚህም ነው ሸንጎ “እኛም ከሚሊዮኞቹ ውስጥ ነን” በማለት በአንድነት አቀነባባሪነት የተጀመረውን እንቅስቃሴ ሙሉ በሙሉ የሚደግፈው። ለዚህ ነው ሸንጎው ሁሉም ኢትዮጵያዊ የዚህ የነፃነት ትግል አካልነቱንና አጋርነቱን በተግባር እንዲያሳይ በቀጣይነት የሚጥረውና የሚያበረታታው።

አንድነት ኃይል ነው! 
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ! 

No comments:

Post a Comment