Friday, May 10, 2013

የቃሊቲው ደብዳቤና የርዕዮት እውነቶች



ሚያዝያ 23 2005 ዓ.ም ሪፖርተር ጋዜጣ በቅጽ 18 ቁጥር 44/1356 ዕትሙ “በህግ ታራሚ ርዕዮት ዓለሙ ላይ የደረሰ አንዳችም አይነት ችግር የለም!” በሚል ርዕስ ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት አስተዳደር የተላከ ደብዳቤ አስነብቧል፡፡ ደብዳቤው በቅጥፈትና በክህደት የተሞላ ነው፡፡ ከዚህም በላይ ባልተነሳ ጥያቄና ባልተባለ ነገር ላይ በማተት የተነሳበትን ሀቀኛ ጥያቄ አደናብሮ ለማለፍ ከአንድ ህገ መንግስታዊ ተቋም የማይጠበቅ ጥረት አድርጓል፡፡ ይህ የሆነውም ርዕዮት ራሷን በማትከላከልበት ሁኔታ ውስጥ መሆኗን እንደ መልካም አጋጣሚ በማየት ይመስላል፡፡ በመሆኑም በደብዳቤው ላይ የሰፈሩትን አብዛኞቹን ጉዳዮች በቅርብ ስለማውቃቸው የርዕዮትን እውነቶች የማስረዳት ሞራላዊ ኃላፊነት እንዳለብኝ በማመኔ ይህን ጽሑፍ ለማዘጋጀት ተገድጃለሁ፡፡Reeyot-Alemu
በደብዳቤው ከታጨቁ ቅጥፈቶችና ማወናበዶች መሐከል ጸሐፊውን ጠልፈው የሚጥሉ እውነቶች ተሸሽገው ቀርበዋል፡፡ ከነዚህም መሐከል አንደኛው ርዕዮት ለብቻዋ እንድትታሰርና በጠያቂዎቿ እንዳትጎበኝ ለማድረግ ማረሚያ ቤቱ እንደተዘጋጀ ማረጋገጡ ነው፡፡ በደብዳቤው መጨረሻ ላይ፣
‹‹በማረሚያ ቤት አብረዋት ከሚኖሩ ታራሚዎች ለመረዳት እንደቻልነው ርዕዮት ያለምንም ጥረትና ልፋት ዝናን ለማግኘት በመሻቷ ከታራሚዎችና ከጥበቃ አባሎች ጋር በየጊዜው ትጋጫለች፡፡ ጤናማ የሆነ ግንኙነት የላትም፡፡ በተለያየ ጊዜ በታራሚዋ ላይ የዲሲፒሊን ግድፈት በመታየቱም ማረሚያ ቤቱ ጥፋቱን በማጣራት ላይ ይገኛል፡፡ ጥፋተኛ ሆና ከተገኘችም በፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የሕግ ታራሚዎች መተዳደሪያ ደንብ ቁጥር 138/1999 መሠረት ተገቢውን የዲሲፒሊን እርምጃ ተቋሙ እንደሚወስድ ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡›› የሚል ሀሳብ ሰፍሮ ይገኛል፡፡
በጽሑፉ ላይ እንደሚታየው ርዕዮት የዲሲፒሊን ግድፈት ማሳየቷን ማረሚያ ቤቱ ደምድሟል፡፡ ከዚህም በላይ ከጥበቃ አባሎችና ከታራሚዎች ጋር እየተጋጨች የዲሲፒሊን ግድፈቱን የምትፈጽመው ለምን እንደሆነ ሲገልጽ “ያለምንም ጥረትና ልፋት ዝናን ለማግኘት በመሻቷ ከታራሚዎችና ከጥበቃ አባሎች ጋር በየጊዜው ትጋጫለች፡፡ ጤናማ የሆነ ግንኙነት የላትም፡፡” በማለት በልቧ ምን አስባ ድርጊቱን እንደምትፈጽም ሁሉ መቶ በመቶ እርግጠኛ ሆኖ ነግሮናል፡፡ ታዲያ ማረሚያ ቤቱ የሚያጣራው ምንድን ነው? ጥፋተኝነቷን ከነ መንስዔው እርግጠኛ ሆኖ እየነገረን፤ መልሶ ደግሞ ጥፋተኛ ሆና ከተገኘች እርምጃ እወስዳለሁ ማለቱ አልሞ ለመተኮስ ሳይሆን፣ የሚፈልገው ላይ ተኩሶ ዒላማ ለማክበብ መዘጋጀቱን ያሳብቃል፡፡


አርሶ መራብና ተኩሶ መሳት፣
እያደር ይፈጃል እንደእግር እሳት! ሆነበት እንጂ ነገሩ፡፡
ማረሚያ ቤቱ ከሳሽም፤ አጣሪም፤ ፈራጅም፤ እርምጃ ወሳጅም ሆኖ መቅረቡ ደግሞ “በህግ ሽፋን ርዕዮት ብቻዋን እንድትታሰርና ጠያቂዎቿ እንዳይጎበኟት ለማድረግ እየሰራ ነው” የሚለው ስጋት እውነት መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ሲፒጄም ቢሆን ያለው ይህንኑ ነው፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ በደብዳቤው ላይ፤
በአንዳንድ ሚዲያዎች የተገለጸው ሌላው ጉዳይ ለሁለት ወራት በአንድ ክፍል ውስጥ ለብቻዋ እንደታሰረች የሚገልጸው ዘገባ ነው፡፡ ይህ ዘገባ ከርዕዮት ጋር የሚኖሩ የህግ ታራሚዎችን ከመናቅ ወይም እንደሰው ካለመቁጠር የመነጨ ይመስለናል፡፡ ሀሳቡ የርዕዮት ከሆነም ለራሷ ካላት የተጋነነ ግምት ወይም ማንነት የመነጨ ሊሆን ይችላል፡፡ የሚል ውንጀላ ቀርቧል፡፡
እግዜር ያሳያችሁ! “ሊሆን ይችላል” ነው ያለው፡፡ ግምት ብቻ ተይዞ “ለራሷ ካላት የተጋነነ ግምት… እንደሰው ካለመቁጠር የመነጨ” የመሳሰሉ ሥነልቡናዊ ትንታኔዎች ውስጥ እንዴት ይገባል? ኧረ ጎበዝ አታሳፍሩን!
እርግጥ ነው ርዕዮት ለብቻዋ እንድትታሰር ሊያደርጋት በሚችል አንቀጽ (በፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የሕግ ታራሚዎች መተዳደሪያ ደንብ ቁጥር 138/1999) ክስ ተመስርቶባት ውሳኔውን (ውሳኔው ተግባራዊ የሚሆንበትን ዕለት) በመጠባበቅ ላይ ናት እንጂ በአሁኑ ሰዓት ለብቻዋ አልታሰረችም፡፡ ለዚህ ጉዳይ ሽፋን ከሰጡ በርካታ የሀገር ውስጥ የህትመት ውጤቶች መሐከል አንዱ (ሪፖርተር ጋዜጣ ቅጽ 18 ቁጥር 42/1352) ‹‹ርዕዮት ለብቻዋ ታስራ ትገኛለች›› ብሎ ሲፒጄ መናገሩን ጽፏል፡፡ ማረሚያ ቤቱን ለግምታዊ ስህተት የዳረገውም ይሄው ዘገባ ነው፡፡ ነገር ግን እንኳን አንድ ትልቅ ተቋም ቀርቶ፤ የዘገባው ስህተት ከምን የመነጨ እንደሆነ ማረጋገጥ የሚፈልግ ሰው የሲፒጄን ኦርጂናል መግለጫ ማንበብ፤ አሊያም ጋዜጣውን መጠየቅ ብቻ ይበቃዋል፡፡
እኔ ያነበብኩትና ለፌደራል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን በአድራሻው የተላከት የሲፒጄ ደብዳቤ “ርዕዮት ለብቻዋ ታስራለች” አይልም፡፡ በጉዳዩ ላይ መረጃ የሰጡ የርዕዮት ቤተሰቦችም በአንድም ሚዲያ ላይ ይህን አላሉም፡፡ ታዲያ ሪፖርተር ከየት አመጣው? የሚለውን ጥያቄም ከጋዜጣው በስተቀር ርዕዮትም ሆነች ማንም ሰው ሊመልሰው አይችልም፡፡
ከዚህ ሌላ ርዕዮት ማረሚያ ቤቱ እንዳለው አይነት ሰው አለመሆኗን ዓለም የሚያውቀው እውነት በመሆኑ ይህን ለማስረዳት አንዲትም ቃል ሳላባክን ወደ ቀጣዩ ርዕሰ ጉዳይ ልለፍ፡፡
ህክምናዋን በተመለከተም ምንም አይነት ችግር እንዳላጋጠማት በደብዳቤው ላይ ተገልጿል፡፡ “ማረሚያ ቤት በቆየችባቸው ጊዜያት በተለያዩ ቀናት ወደ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ተልካ ሕክምና ማግኘቷን ከግል ማህደሯ ማረጋገጥ ይቻላል” በማለትም እማኝ ይጠቅሳል፡፡
በተለያዩ ቀናት፣ ወደ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል መሄዷ እውነት ነው፡፡ ነገር ግን በጡቷ ላይ ሕመም እንደሚሰማት ተናግራ ሪፈር እንዲጻፍላት ብትጠይቅም፣ ከመንፈስ ጭንቀት ውጪ ምንም በሽታ እንደሌለባትና የእጅ ሥራ እንድትሰራ፤ ጥልፍ እንድትጠልፍ ስትመከር መሰንበቷ፤ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ሄዳ ህክምናዋን ለመከታተል የቻለችውም ከብዙ አቤቱታ በኋላ ኦማር የተባለ የአፍሪካ ጋዜጠኞች ፌዴሬሽን ተወካይ ከአንድ ኢትዮጵያዊ ጋር ቃሊቲ ድረስ ሄደው በጎበኟት ወቅት በእነሱ በኩል በቀረበ አቤቱታ በማረሚያ ቤቱ ዋና አስተዳዳሪ ትዕዛዝ መሆኑ ቢታከልበት የተሻለ እውነት ይሆን ነበር፡፡
ሕክምናዋን በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል መከታተል ከጀመረች ወዲህም ብዙውን ጊዜ በቀጠሮዋ መሠረት ተገኝታ መታከም አለመቻሏ፤ ህመሟ ጊዜ የማይሰጥ በመሆኑ የተለየ ህመም ካጋጠማት ቀጠሮዋን ሳትጠብቅ ወደ ሆስፒታል እንድትመጣ በሀኪሞቹ ቢታዘዝም፤ ከጥር 10 ቀን ጀምሮ ክፍተኛ ደም ከጡቷ እየፈሰሰ እስከ የካቲት 07 ድረስ ህክምና ሳታገኝ በስቃይ መክረሟ፤ ከዚያ በኋላም ሀኪሟ በአስቸኳይ የናሙና ምርመራ ተደርጎ የዕጢው ደረጃ ከታወቀ በኋላ መለስተኛ ቀዶ ጥገና ማድረግ እንደሚኖርባት በመግለጽ ለየካቲት 13 ቀጠሮ ቢሰጥም መኪና የለም በሚል ሰንካላ ሰበብ እስከ መጋቢት 2 ድረስ፣ ከነስቃይዋ እንድትቆይ መደረጓና ሌሎች ታራሚዎች ህክምናቸውን ሲከታተሉ የቀጠሯቸው ቀን ከፍርድቤትና ከሌሎች ቀጠሮዎች ጋር እንዳይጋጭ የህክምና ቀጠሯቸውን እዚያው ሆስፒታል እያሉ እንዲያውቁት የሚደረግበት አሰራር የተለመደ ሆኖ እያለ ርዕዮት ከመጋቢት 2 ወዲህ መቼ ምን አይነት የሀኪም ቀጠሮ እንዳላት ለማወቅ ብትጠይቅም፣ በግልጽ ‹‹ለአንቺ አይነገርሽም›› መባሏ ተገልጾ ቢሆን ኖሮ ሙሉ እውነት ይሆን ነበር፡፡
ፍጹም እውነት እንዲሆን ደግሞ… እንጂማ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል መሄዷ ብቻ ሳይሆን መለስተኛ ቀዶ ጥገና አድርጋ ከጡቷ ላይ ዕጢ ማስወጣቷም ጭምር ከወራት በፊት ሁሉም የሰማውና ያረጀ ዜና ነው፡፡
የትምህርቷን ጉዳይ በተመለከተ ከመነሻው ጀምሮ እስከ ክልከላው ድረስ እኔ ራሴ ስከታተለው የነበረ በመሆኑ፣ ማረሚያ ቤቱ ላከ በተባለው ደብዳቤ ላይ ያነበብኩት ነገር ክፉኛ አስደንግጦኛል፡፡ ጸሐፊው ትክክለኛ መረጃ ሳያገኝ በየዋህነት ተሳስቶ ካልሆነ በቀር እንዲህ አይነት አይን ያወጣ ቅጥፈት በአደባባይ እንዲነበብ ለመጻፍ በገዛ ህሊናው ላይ የሰለጠነ ልዕለ ኃያል ሰው መሆን ይጠይቃል፡፡
የሆነው ሆኖ “ትምህርቷን እንድትከታተል የሴቶች ቀጠሮና ማረፊያ ቤት ተገቢውን ድጋፍ እያደረገላት ይገኛል፡፡” ተብሎ የተገለጸው ፍጹም ሀሰት ሲሆን እውነቱ የሚከተለው ነው፡፡
የማረሚያ ቤቱን ይሁንታ ጠይቃ ካገኘች በኋላ ህዳር 29 2012 እ.ኤ.አ ያስመዘገብኳት እኔው ራሴ ነበርኩ፡፡ መመዝገቧን ካሳወቀች በኋላም ጉዳዩ የሚመለከታቸው የማረሚያ ቤቱ ባልደረቦች ት/ቤቱ ድረስ በመሄድ እንዳረጋገጡ የሰማሁት ከራሳቸው አንደበት ነው፡፡ በየካቲት ወር መጨረሻ ትምህርቱ ሲጀመር የመማሪያ መጻህፍቶቿን ይዤ በሄድኩበት ጊዜ ግን የተሰጠኝ “እሷ እንድትማር አልተፈቀደላትም” የሚል ምላሽ ነው፡፡ ጉዳዩ እስካሁን ድረስ እልባት ባለማግኘቱ ትምህርቷን መጀመር አልቻለችም፡፡ የመማሪያ መጻሕፍቱም እስከ ዛሬ ድረስ በእጄ ይገኛሉ፡፡
በመጨረሻም መሽቶ በነጋ ቁጥር በሁሉም መስክ የባሰ ነገር መጋፈጥ ልማዳችን ነውና ለማረሚያ ቤቱ ደብዳቤ ይህን ያህል ጊዜና ጉልበት ከፈጀን በቂ ነው፡፡ ነገ ለሚመጣው የባሰ ነገር ጊዜና ጉልበት መቆጠብ፣
ያምናን ቀን አማሁት ላፌ ለከት የለው፤
የዘንድሮው መጣ እጅ እግር የሌለው፡፡
የሚል ቁዘማ ውስጥ ከመዘፈቅ ሳያድነን አይቀርም፡፡
ቺርስ!

No comments:

Post a Comment