Friday, May 10, 2013

ያበቃለት ስርአት








አንድ ስርአት ሕይውት አለው(alive) ይሠራል(working/Functional) ጥሩ ይንቀሳቀሳል(Vibrant) የሚባለው እንደ ስርአት፤እንደ መንግሥትና እንደ መልካም አስተዳደር ማድረግ የሚገባውን ሲያደርግ ነው። በየትኛውም ቦታና ጊዜ የአንድ መንግሥት አይነተኛ ተግባር፤ለእድገት ለብልጽግና ለሰላም ለደሕንነትና ለለመለመ ተስፋ አስፈላጊውን ሁኔታውች መፍጠር ነው። አንድ መንግሥት እንደ እድገት ደረጃዎቹ በተለያ ጊዜ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን መሥራት ቤገባውም፤እዝብን ተክቶ በጅምላ ተቆጣጥሮ እራሱ መሥራት አይገባውም ቢሠራም የሚያሰኬድ አይሆንም፤ከግል ጥቅም ባለፈ፤የተፈለገውንም እድገትና ብልጽግና ለማምጣት አይችልም። ሁሉም ቀና መልካምና ተገቢም የሚሆነው መንግሥት በሞኖፖል ሁሉን በመቆጣጠር ሳይሆን ነጻና ሕዝብን ያሳተፈ የህዝብ ቀዳሚ አለኝታነት ያለው መሰረተ ሰፌ የግንባታ ሥራ ሲሠራ ነው።
አንድ ስርአት ህይወት አለው ለማለት የሚያስችሉ መመዘናዎቹ ምን መሆን አለባቸው የሚለውን ስንመልስ ህያውለቱን ወይም ሙትነቱን ማስቀመጥ እንችላላለን። መኖር ከተባለ ቆሞ የሞተ፤ሕይወት እያለው በድን የሆነ ስርአትም አለ። በቀላሉ መኮፈሱ ሕይወት አለው ለማለት ዋስትና አይሆነውም ለማለት ነው።አንድ ስርአት የሚሠራና ህይወት አለው የሚባለው፦

1. በተለያዩ ዘርፍች የሕዝብን ፍላጎት ሲየሟላ፤
2. የህዝብን መብት ሲያስከብር/ሲያስከብር፤
3. የአገርን፤የህዝብን ደሕንነት ሕልውናና ሰላም ሲያረጋግጥ፤
4. ለእድገትና ብልጽግና አስፈላጊ ሁኔታዎችን ሲፈጥር፤
5. በአጠቃላይ እድገትን ሲያመጣ፤
6. የነገን ተስፋ ሲያለመልም፤
7. የሕዝብን ስነልቡና ስነአእምሮና የሞራል ደሕንነትን ሲንከባከብ ነው።
በአጠቃላይ ለሕዝም፤ለአገር፤ለትውልድ ይበጃሉ የሚባሉትን መልካም መልካሙን ሲያስብ፤ሲያቅድና ሲደነግግ በተከታታይ በዘላቂነት ሲያስፈጽም፤ሲያግዝና ሲያመቻች አንድ ስርአት ሕይወት አለው ለማለት ይቻላል።
በአሁኑ ጊዜ በአገራችን ያለው ስርአት እነዚህ ከላይ የተዘረዘሩትን ፈጽሟል ለማለት የሚደፍረ ቀርቶ የሚያስብ አለ ለማለት ይቸግራል። ከሕዝብ የቀን ተቀን ፍላጎቶች እስከ መብትና ነጻነቱ፤ከአገር ሕልውናና ዘለቄታ መረጋገጥ እስከ እድገትና ብልጽግና፤ከሰብአዊ መብት መረጋገጥና እስከ ስነልቡና ነጻነት ወዘተ. አንዱም አሉ ለማለት አይቻልም።
በአንጻሩ የሚታየው-የህዝብ ፍላጎት መሟላት ሳይሆን የኑሮ ማሽቆልቆል፤እድገት አልባነት፤የነገው ተስፋ የተዳፈነበት፤የአገር የሕዝብ ሕልውና አደጋ ላይ የወደቀበት፤የሕዝብ መብትና ነጻነት የታፈነበት፤የህዝብ ልጆች በአፈና ወደእስር የሚጋዙበት፤አይነተኛው መሰረታዊው የሕዝብ የእድገትና የብልጽግና እጅ የታሰረበት፤ሕዝብ በፍረሀት በጭንቀት፤በውጥረት፤በስጋት የሚኖርበት ሁኔታ ነው።
አነዚህ መመዘኛዎች በአገራችን ያለውን ስርአት ያበቃለት፤የሞተ፤በድን፤ በሙቱ የሚንቀሳቀስ አድርገውታል።ይህን አሌ የሚል በጥቅም የታወረ፤በእምሮው ሳይሆን በሆዱ፤ለሕዝብ ሳይሆን ለራሱ፤ለአገር ሳይሆን ለግሉ፤ለትውልድ ሳይሆን በእለት ጥቅም የተጠመደና የታወረ አስተሳሰበ ጎደሎ ብቻ ነው።
ሚዛን ወርቅንም ጠጠርንም፤ዱቄትንም አፈርንም፤ብረትንም ድንጋይንም–ወዘተ ለመመዘን ይረዳል። የትላንቱ የቀደመው የስርአት ማብቂያ መመዘኛዎች ዛሬም አይነተኛ መመዘኛዎች ናቸው። በዚሁ ሂደት ስርአቱ አበቃለት ሲባል፦
1. ሕዝብን አገርን መምራት ማስተዳዳር ተስኖታል፤
2. ሕዝብ በነበረው መቀጠል አልፈለገም፤መሮታል ስርአቱን ክዶታል አንቅሮታል፤አመቺ ጊዜ ይጠብቃል፤
3. በእነዚህ ምክንያቶች ቀውስ ተፈጥሮአል፤የሕዝብ የመኖርር ተስፋው ጨልሟል አመጽ በያይነቱ ቀጥሏል፤አደጋ አንዣቧል ማለት ነው።
እነዚህ ጊዜ የፈተናቸው አሁንም ወደፊትም የሚያገለግል የመመዘኛ መሳሪያዎች ናቸው።
ሕዝቡ በተግባር የሚያስተባብረውን እስከሚያገኝ ድረስ በልቡ ሸፍቷል፤በስርአቱ ላይ አመኔታ አጥቷል፤የመገላገያ ጊዜው እየተፋጠነለት መሆኑን ተረድቶ ስነልቡናዊ ዝግጅት እያደረገ እየተጠባበቀ ነው።በዚሁ መጠን ስርአቱ እንደለመደው ዓይኑን በጨው ታጥቦ በዝርፊያው፤በአፈናው፤መማሳሳቱ፤በመዋሸቱ፤በማስተባበሉ፤በአገር ትውል አውዳሚ ተግባሮቹ አየቀጠለበት ሲነጉድ ይታያል። የተስፋ መቁረጥ ምልክቶች። ከዛሬ ነገ አበቃልን ብቻ ሳይሆን ያመለጠውና በጊዜ የተሳናበታቸው እንዳለ ሆኖ፤አገር ጥሎ ንብረት ጠቅልሎ ቤተሰብ አንጉዶ ለመውጣት የተዘጋጀውም የበረከተ ነው። ከፊሉም የትም ቦታ ቢሄድ የትም፤እስከዛሬ ሲገል ሲያስርና ሲያሳድደው የነበረው ወገን እንደሚጠብቀው አውቆ ስልጣን ሙጥኝ ብሎ መጺአ እድሉን እየተጠባበቀ ነው። የስርአቱ ቀንደኛ አራማጆች፤በስልጣን ላይ ካልሆነ ለመኖር ተስፋ ያጡበትን ሆኔታ ያመላክታል።
ይህ ሆኖ ሳለ አበቃለት፤ሙት ነው፤ደመ ነፍሱን እንጂ በድኗል ሲባል የሚያስነሳው ጥያቄ -አንዴት እስከዛሬ ዘለቀ ነው። ለነገሩማ ስርአቱ ያበቃለት ከበፊቱና በ2005 ነው። ከሞት አፋፍ ደርሶ ሲያጣጥር ማን እስትንፋስ ሰጥቶ ነፍስ እንደዘራለት፤እንዳሰነበተው አሁንም በተለያየ ዘርፍ ንዋይ እያጎረፈ እያጠነከረ እንዳዘለቀው ለሁሉም ግልጽ ነው። ለምን ቢባል ከአገር ጥቅም ይልቅ የባእድ ጥቅም አስከባሪ ስለሆነ፤እነርሱም ይህን ሲለሚያውቁ፤ከጫካ ጀምረው ያሳደጉት ሚስጥራዊ መረጃዎችን በየጊዜው እስከ አሁን ድረስ የሚመግብ የሚመገብ መሆኑን መጥቀስ ባላስፈለገም ነበር። በዚሁ ሂሳብ ብሔረተኛ አገር ወዳድና ለራስ ጥቅም ያልተገዙ ወገኖች እንዴት ከመጀመሪያው ሲገለሉ እንደቆዩም ሂሳብ ውስጥ መግባትም አለበት። በጅምላ አመለካክት ስርአቱ ሊቀጥል የቻለው፤በሞቱ አለሁ የሚለው በመልካም ሥራው ሳይሆን በአጠቃላይ መልኩ ፦
1. በአፈና፤
2. ሑሉን አውታሮች በጅምላ በመቆጣጠር፤
3. በመከፋፋል፤በማናቆር፤በማጋጨት፤
4. በማደህየት፤
5. እጅ እግር በሌለው በውሸት የፐሮፐጋንዳ ዘመቻ፤
6. በተወካይ የጥቅም አስከባሪነትና፤
7. በተረካቢ እጦት ነው።
ብዙ ሌሎችም ሊጠቀሱ ይችላሉ። እነዚህን የሚጠቀምባቸው ዛሬን የመዋያና የማደሪያ ስልቶቹ ሲሆኑ፤እላይ እንደተጠቀሰው የተስፋ መቁረጥ፤የዘላቂ ተስፋ ማጣት ምልክቶች እንጆ የመልካም አስተዳደር መሳሬያዎች አይደሉም።
ዘረፋ፤ንዋይ ማሸሽ፤አገርን ላደጋ ማጋለጥ፤የተውልድ ተስፋ ማምከን፤አገርን ማውደም፤መሸጥ አይነኛ የተስፋ መቁረጥ የሞራል ዝቅጠት፤የቂም በቀልና የጥላቻ፤የስግብግብነትና ጭፍንተኝነት ምልክቶች ናቸው።
እንደ እውነቱ ከሆነ፤ስርአቱ ካበቃለት ቆይቷል፤የብድር ጊዜውንም ከጨረሰ አመታት አልፈዋል።ስርአቱ የሞተው፤የሞተው የሞተ ጊዜ ነው። የእከሌ መንግስት እከሌ ሲሞት አብሮ ሞቷል። እንደ እከሌ ሊያስቀጥል የሚችል፤እከሌም እከሌንም የሚመስል ሰንኮፍ የለም።
ነገሩ የቆሰለ አውሬ በቅጡ ማሰብ አይችልም፤ያገኘውን ሁሉ ይነግሳል፤በደመነፍሱ ያለም እንዲሁ፤የሚያምነው የሌለው ጥላውንም ይፈራል-መልእግቱ ግልጽ ነው። የባስ ብሎም እሳካሁን ሲጠጋግኑት የነበሩትም ወድቆ ዓይናቸው ካላየና ምንም ሊያደርጉ የማይችሉበት ደረጃ ካልደረሱ ፊታቸውን አይመልሱም፤መጠጋገናቸውን በሁሉም መስክ ለስርአቱ መቸራቸውን አያቆሙም፤የታየ ነው።ይህ ሀቅ በቅጡ ግንዛቤ ሊያገኝ ይገባዋል። የስርአቱ ሕልውና ያለው በአብዛኛው እዚህ ላይ ነውና።
ዞሮ ዞሮ ቢደጋገምም አንድ የማይቀር ጉዳይ መጠቀሱ የግድ ነው። ስርአቶስ በግብታዊም ሆነ በተቀናጀ አመጽ ሲያከትም፤የማትቀረዋ ቀን ስትቀርብ ማን ይተካው ነው። በዚያች ወቅት ፖለቲካ እንደወግ ሳይሆን የምር ይሆናለች። ሁሉም ባመቸው በመረጠው በፈቀደው መንገድ ሊታገል መብት አለው። በአይነተኛ የሕዝብን ደሕንነት መብትና ነጻነትን፤የአገርን አንድነትና ሕልውና በተመለከቱ መሰረታዊ ነጥቦች ላይ በመስማማት ለመቀጠል ከሁሉም በላይ አንድንት የሚመረጥ ቢሆንም፤በአንድነት ስም የማያራምድ ለአሠራር ችግር በሚፈጥር በማያንቀሳቅስ ሂደት ከመጠፈር፤በሀሳብ በተግባር መተባበር፤ከሽኩቻ መታቀብ ተገቢና አማራጭም ነው።
ከሰላማዎ መንገድ፤የለመዱትን የመሳሪያ ሐይል ከመረጡላቸው አደጋውን ማሰብ ተገቢ ነው። አንድነት ካለ ቀናቶች ያጥራሉ መከራ ፈተና ይቀላል ዘላቂውም የሰምራል። ግራም ነፈሰ ቀኝ ወቅቱ መተባበርን፤አንድነትን፤አቅም መገንባትን፤ማቀድን፤ለማያዳግመው መዘገጃጀትን ይጠይቃል። እንደ ዶሮ ጨጩት ከላይ እሰከታች ከፓለቲካ እስከ ሐይማኖት ከማሕበራዊ አስከ—-በሰላማዊውና በሁለገብ መስክ የተሰማራውን ምርጥ ሓይል ለቅሞ ለእስር ቢዳርግም አገሪቱ በያለት በአገርም በውጭም የሕዝብን ተስፋ ለማለምለም፤ እድገት ብልጽግናን ለማምጣት፤የአገር አንድነትንና ሕልውናን ለማስጠበቅ ለማዝለቅ ብቃት ብስለት ልምድና ችሎታ የሞራልም የበላይነት ያላቸው በርካታ ልጆች አሏት። ለስርአቱ በአፈና የሚወጣው ቢመስለው እንጂ በቀላሉ አገሪቱና ሕዝቡ ንጹህ አሰባሳቢና የአመራር ሰጪ ሰው ሐይል እጥረት የለባትም። ጠቅላላ ሕዝብን ማሰር ደግሞ አይታለምም።
በመጨረሻም ቁምነገሩ እስከዛሬ ሲደከምበት፤ሁሉም በየወቅቱ ሳያሰልስ የታገለው ትግል ፍሬ ማፍራቱ ነው። የሕዝብ ጎራ የድል በለስ ቀናው ማለት ነው። ስርአቱ ተአማኒነቱን ያጣውና የደረሰበት ደረጃ የዘቀጠው በከፊሉ በእራሱ የከፋ ድረጊት ቢሆንም በአመዛኙ ተገቢውን መስዋእትነት ከፍለው በታገሉ የአገሪቱ የክፉና የቁርጥ ቀን ልጆች ነው። በተደረገው ጥረት ስርአቱ እርቃኑን ቀርቷል፤ያለ ቢመስልም አክትሟል ሞቷል፤ደመነፍሱን በሙቱ በበድሉ ይንቀሳቀሳል።
የቀረው የመጨረሻው ግፊት ነው።ሕዝብ በቀላሉ በተቀናጀ መልክ፤ሌሎች አማራጮች እንዳሉ ሆነው፤ በሰላማዊ መንገድ ብቻ ቢያምጽ የማክተሚያው የመፈንገያው ደወል ተደወለ ማለት ነው። ያን ጊዜም ድል ትጸናለች፤ተስፋም ይለመልማል፤ሕዝብ የነጻነት ንጹህ አየር ይተነፍሳል፤በነጻነት ያስባል፤በአማረ የእድገት እርምጃም ይራመዳል፤ዋስትናውም ይረጋገጣል።
ኢትዮጵያ በእግዚአብሔርና በሕዝቧ ተጠብቃ ትኖራለች!
ቸር ይግጠመን!
ፍአ.

No comments:

Post a Comment