Friday, June 27, 2014

ለውጭ ዜጎች ቅምጥ የሆኑ ሴቶች እና ሴተኛ አዳሪ አግብተው የሚኖሩ ወንዶች


ሰላማዊት ከበደ (ስሟ ተቀይሯል)፡፡ በሁለት ዓይነት የፍቅር ግንኙነት ውስጥ ትገኛለች፡፡ ቤት ተከራይቶ ያስቀመጣትና የሚረዳት የውጭ ዜጋ ወጣት አለ፡፡ በሌላ በኩል አፈቅረዋለሁ የምትለው ሌላ ኢትዮጵያዊ ጓደኛም አላት፡፡
ዕድሜዋ አሥራ ዘጠኝ እንደሆነ፤ ከፍቅረኛዋ ጋር ከሦስት ዓመት በላይ አብረው መቆየታቸውን ትናገራለች፡፡ እሷ እንደምትለው ከውጭ ዜጋው ወዳጇ ጋር ከተገናኙ ከአንድ ዓመት በላይ ሆኗል፡፡
ታላቅ እህቷ የውጭ ዜጋ ወዳጅ ነበራት፡፡ በዚህም በተደጋጋሚ ወደ ውጭ ትመላለስ ነበር፡፡ ደህና ሊባል የሚችል ገንዘብም ነበራት፡፡ ቤተሰባቸው በጣም ችግረኛ የሚባል ያልነበረ ቢሆንም የታላቅ እህቷ ከውጭ ዜጐች ጋር ወዳጅነት በመመሥረትና ገንዘብ ማግኘት የቤተሰባቸውን ይሁንታ አግኝቶ ነበር፡፡ ዛሬም ታላቅ እህቷ የአንድ የውጭ ዜጋ ቅምጥ ስትሆን ሐበሻ የወንድ ጓደኛም አላት፡፡ በዕድሜ የገፋው (ሰባ ዓመት) የውጭ ዜጋ ወዳጇ ሕልፈተ ሕይወትን እሷም ፍቅረኛዋም በጉጉት እንደሚጠባበቁ በተለያየ ጊዜ በግልጽ ስትናገር ትደመጣለች፡፡

‹‹እህቴ በዚህ ዓይነት ገንዘብ ማግኘት በጀመረችበትና በአጭር ጊዜ ውስጥ መኪና በገዛችበት ወቅት ተማሪ ነበርኩ፡፡ በዚያ ጊዜ ፍቅር ውስጥ ነበርኩ፡፡ እናቴ ፍቅር ውስጥ መሆኔን በመኮነን እህቴን እንድመለከት ዘወትር ትናገረኝ ነበር፡፡ እኔም የእናቴ ግፊት ስለበዛብኝ ገንዘብ ለማግኘት፤ ዘና ብሎ ለመኖርም እህቴ ታዘወትርበት የነበረ ቤት አዘውትሬ ከአምስት ጓደኞቼ ጋር መሔድ ጀመርኩ፤›› የምትለው ሰላማዊት፣ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ እሷን ጨምሮ ከአምስቱ ጓደኛሞች ሦስቱ ከውጭ አገር ዜጐች ጋር የጠበቀ ግንኙነት መመሥረት መቻላቸውን አስታውሳለች፡፡
ዛሬ እሷም ታላቅ እህቷ በምትገኝበት የፍቅርና የጥቅም ግንኙነት ውስጥ ትገኛለች፡፡ ከውጭ ዜጋው ወዳጇ የሚገኘውን ማንኛውንም ዓይነት ጥቅም ከፍቅረኛዋ ጋር ይጋራሉ፡፡ ወዳጇ በተወሰነ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ከመመላለስ በስተቀር ቋሚ ኑሮው ውጭ አገር በመሆኑ ሁለቱንም ግንኙነቶች ጐን ለጐን ማስኬድ ብዙም እንዳልከበዳት ትገልጻለች፡፡ ነገሮች በተወሰነ መልኩ አስቸጋሪ የሚሆኑት የውጭ ዜጋ ወዳጇ እዚህ በሚኖርበት ጊዜ ነው፡፡ ‹‹ስልኬ ላይ ምንም ዓይነት ነገር እንዳይገኝ እጠነቀቃለሁ፡፡ መደዋወልም ሆነ መልዕክት መላላክ የሚያደርገው በጥንቃቄ ነው፡፡ ቢሆንም ጓዳኛዬን ማግኘት ስለማልችል እሱ እዚህ በሚሆንበት ጊዜ ነገሩ ይከብደኛል፤ ያስጠላኛልም፡፡››
ፍቅረኛዋ ምንም ዓይነት ሥራ አይሠራም፡፡ እሷም እንደዚሁ፡፡ ነገር ግን በተለያየ መመዘኛ ኑሯቸው ጥሩ ሊባል የሚችል ነው፡፡ ፍቅረኛዋ ከእሷ ጋር ወደፊት አብሮ የመኖር ራዕይ እንዳለው እሷ የምትወደውን ያህል እንደሚወዳት አንዳችም ጥርጣሬ እንደሌላት በልበ ምሉነት ትናገራለች፡፡
በአንድ በኩል ከውጭ ዜጋው ወዳጇ በሌላ ጊዜ ደግሞ ከፍቅረኛዋ ጋር በተለያዩ አጋጣሚዎች አብራ ለሚመለከቷት ሰዎች ማን ምኔ ነው? እንደምትል ሰላማዊትን ጠይቀናታል፡፡
የምትደብቀው ምንም ነገር እንደሌለ፤ ከውጭ ዜጋው ጋር ለገንዘብ ብቻ ስትል አብራው እንደሆነች በግልጽ እንደምትናገር፣ ቤተሰብና የቅርብ ጓደኞቿም ሁሉንም ነገር በግልጽ እንደሚያውቁና እንደሚረዷት ጭምር ነግራናለች፡፡
ሰላማዊት በሕይወቷ ደስተኛ ስለመሆኗ በማስመልከት ላነሣንላት ጥያቄም፣ ‹‹አሁን በሕይወቴ ደስተኛ ነኝ፤ ነገር ግን ይበልጥ ደስታዬ ሙሉ የሚሆነው ከፍቅረኛዬ (ከሐበሻው) ጋር ብቻ መኖር ስችል ብቻ ነው፤›› ብላለች፡፡
በሕጋዊ መንገድ ጋብቻቸውን ፈጽመው ለሦስት ዓመታት አብረው ኖረዋል፡፡ አንድ ልጅም አላቸው፡፡ እሷ ሴተኛ አዳሪ ነች፤ እሱ ደግሞ ዲጄ ነበር፡፡ አሁን ግን ምንም ዓይነት ሥራ አይሠራም፡፡ ለምን? ብለን ጠየቅነው፡፡ ‹‹በተለያዩ ቤቶች ውስጥ ስሠራ በተለያዩ ጊዜያት ሴተኛ አዳሪ ፍቅረኞች ስለነበሩኝ አብረን ለመኖር ስንወስን ሥራ እንዳቆም ጠየቀችኝና ተስማማሁኝ፡፡››
ስሙ እንዲጠቀስ ያልፈለገው ይህ ዲጄ፣ ሚስቱንና የልጁን እናት እንደሚወዳት ይናገራል፡፡ እኛም እንደዚህ ያለ ስሜት ካለው የእሷን ዛሬም ሴተኛ አዳሪ ሆኖ መቀጠል እንዴት በቀላሉ ሊቀበለው እንደቻለ ጠየቅነው፡፡ በፊት ቡና ቤት ውስጥ እንደነበር የምትሠራው፤ ከተጋቡ በኋላ ግን በስልክ በደንበኝነት እየተደወለላት እንደምትሠራ ገለጸልን፡፡ ገንዘብ ሊያገኙ የሚችሉበት ሌላ ምንም ዓይነት መንገድ ስለሌለ ነገሩ ብዙም ሳይከብደው ሊቀበለው መቻሉንም ነግሮናል፡፡
እሱ እንደሚለው፣ ሚስቱ በአንድ ሥራ ያገኘችው ገንዘብ አነሰ ከተባለ ከ500 ብር አይወርድም፡፡ በእሱ በኩል የሚመጣ ምንም ዓይነት ገቢ ባለመኖሩ መኖርያቸው የእሷ ሴተኛ አዳሪነት ብቻ ነው፡፡ በዚህ የቤት ኪራይ፣ የሕፃን ትምህርት ቤት፣ ምግብ ሌሎችም ወጪዎች ይሸፈናሉ፡፡ እሱም ስለሚቅምና ስለሚያጨስ በቀን በቀን ለሱ ሃምሳ ብር መመደብም የግድ ነው፡፡ አንዳንዴ በገንዘብ እንደሚጋጩም አልደበቀም፡፡
ከተወሰኑ ሰዎች ውጭ በቅርብ የሚያገኘውና የሚያጠያይቀው ሰው የለም፡፡ ይልቁንም ግንኙነቱ በጣም ውስን ነው፡፡ የሚቀራረበው ከሚስቱ ጓደኞችና በእነሱ በኩል ከሚያውቃቸው ጥቂት ሰዎች ጋር ብቻ ነው፡፡ ምንም እንኳ ከልብ እንደሚወዳት ቢናገርም ሚስቱን በተለያየ አጋጣሚ ‹‹ባለቤቴ›› ነች ብሎ ከሰዎች ጋር ማስተዋወቅ አይፈልግም፡፡ ስለኑሯቸውም እውነተኛውን ነገር መናገር ይከብደዋል፡፡ ቢሆንም ኑሮዬ ብሎ ተቀብሎ እየኖረው ነው፡፡
ሌላው ያነጋገርነው ስሙ እንዲጠቀስ ያልፈለገ ጐልማሳም፣ ምንም እንኳ በሕግ ባይጋቡም ከሴተኛ አዳሪ ባለቤቱ ጋር አብረው መኖር ከጀመሩ ስድስት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ከአንዲት ትንሽ እህቱ በስተቀር ማንም ስለትዳር ሕይወቱ የሚያውቀው ነገር የለም፡፡ በአሁኑ ወቅትም ባለቤቱ የሦስት ወር ነፍሰጡር ነች፡፡ እሷም እንደ ዲጄው ባለቤት የምትሠራው በስልክ ነው፡፡ አሁንም መሥራት አላቋረጠችም፡፡
አቶ ዓለሙ አበራ በኮተቤ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ መምህር ናቸው፡፡ የመጀመርያ ዲግሪያቸውን በሥነ ልቦና ሁለተኛውን ደግሞ በልዩ ትምህርት ፍላጐት ሠርተዋል፡፡ አሁንም ፒኤች ዲግሪያቸውን በመሥራት ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ ኤችአይቪን ጨምሮ በተለያዩ ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ይሠራሉ፡፡
ድብቅ የሆነ የሴተኛ አዳሪነት፣ የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት ለወሲብ ዕርካታ የኤሌክትሪክ መሣርያዎችን የመጠቀም ዓይነት ከባህል፣ ከማኅበራዊ እሴትና ከእምነት ጋር የሚጻረሩ አካሔዶች መኖራቸውን በተሳተፉባቸው የተለያዩ ጥናቶች ማስተዋላቸውን ይናገራሉ፡፡ የእነዚህ ከባህል፣ ከማኅበራዊ እሴትና እምነት ጋር ይጋጫሉ የሚሏቸው ድርጊቶች መጀመርና ሥር እየሰደዱ መሔድን መሠረት በማድረግ ምንም እንኳ የሚጠቅሱት ጥናት ባይኖርም፣ በትዳር አልያም ከትዳር በሚስተካከል የፍቅር ግንኙነት ውስጥ ያሉ ሴቶች ሴተኛ አዳሪነትን እንደ ሥራ የያዙበት፤ ተጓዳኞቻቸውም በዚሁ ሥራ ተስማምተው ጥቅም የሚያገኙበት ሁኔታ እንደማይጠፋ ይገምታሉ፡፡
‹‹ከስድስት ዓመታት በፊት በአንድ ከተማ ውስጥ በሴተኛ አዳሪዎች ላይ በተሠራ ጥናት የተለያዩ ኢሞራል ድርጊቶች መኖራቸው ታይቷል፡፡ ወንድ ለወንድ፣ ሴት ለሴት፣ ድብቅ ሴተኛ አዳሪነት አለ፡፡ ከዚህ በመነሣት በመላ አገሪቱ ሁኔታው ምን ሊመስል እንደሚችል መገመት ይቻላል፡፡››
ዝንጀሮ ወንድ ልጇን በጀርባዋ ካዘለችው አባት ዝንጀሮ በቅናት ስለሚገድለው፣ ሴቷን በጀርባ ወንዱን በሆዷ መያዝዋን በምሳሌነት በመጥቀስ እንስሳት እንኳ በደመነፍስ እንዲህ የሚያስቡበት ሁኔታ እያለ፣ አንድ ባልና ሚስት በሴቷ ሴተኛ አዳሪነት በሚገኘው ገቢ ላይ ተስማምተው መገኘት ከባድ የሞራል ውድቀት፣ የማኅበራዊ እሴት መሸርሸርም እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡
እንደ እሳቸው አባባል፣ በእንደዚህ ዓይነት ትዳር ወይም የፍቅር ግንኙነት ውስጥ የሚገኙ ሴቶች የቱን ያህልም የገንዘብና የቁሳቁስ ፍላጐታቸው የተሟላ ሊባል የሚችል ቢሆንም በሕይወታቸው ዕርካታ ያላቸው አይሆኑም፡፡ ‹‹ባል ወይም ፍቅረኛ የምትለው ወንድ እያለ ለገንዘብ ብላ ከተለያዩ ወንዶች ጋር የምትሆን ተመልሳ ደግሞ ወደ ባሏ የምትሔድ ሴት ምንጊዜም በሕይወቷ ደስተኛ ልትሆን አትችልም፡፡ እንዲሁ ለመኖር ካልሆነ በስተቀር ትዳሩም ሆነ አብሮነቱ ትርጉም የሌለው ዕርካታም የማይገኝበት ነው፤›› የሚሉት የሥነ ልቦና ባለሙያው አቶ ዓለሙ፣ በእንደዚህ ዓይነት ግንኙነት ውስጥ ያሉ ማኅበራዊ ግንኙታቸውና ማኅበራዊ ተሳትፏቸው የደከመ እንደሚሆን ያመለክታሉ፡፡ ከጤናና ከሥነ ልቦና አንጻርም የዚህ ዓይነቱ አካሔድ የሚያስከትለው ችግር ከፍተኛ ነው፡፡
ሴቶች ወደ ሴተኛ አዳሪነት የሚገቡበት ምክንያት ሊለያይ ይችላል፡፡ አንዳንዶች ድህነትን፣ ሌሎች ደግሞ የተሻለና የተንደላቀቀ ሕይወት መፈለግን በምክንያትነት ይጠቅሳሉ፡፡
ባለንበት የወንድ የበላይነት በነገሠበት የማኅበረሰብ ሥርዓት፣ የገንዘብ አቅምን ጨምሮ የሴቶችን ጠንካራ ወይም የበላይ መሆን ተጓዳኞች መቀበል ሲቸግራቸው፤ ይህ የሴቶች በኢኮኖሚና በሌሎችም ጉዳዮች ጠንካራ መሆን ዘወትር በትዳር የግጭትና ያለመግባባት መሠረታዊ ምክንያት ሆኖ ይስተዋላል፡፡
እንደ እሳቸው እምነት፣ የጓደኛው ወይም የባለቤቱ ሴተኛ አዳሪ መሆንን እንደ ማንኛውም ሥራ የሚመለከትና በዚህ መልኩ የሚመጣው ጥቅም የሚያስደስተው ግለሰብ አእምሮ ጤነኛ አይደለም፡፡ ሴቷን ለጥቅም ለወሲብ ፍላጐት እንጂ በፍቅር ያስባታል፤ ወልደን ወደፊት አብረን እንኖራለን የሚል ተስፋ ወይም ራዕይም ይኖረዋል ተብሎ አይታሰብም፡፡ በዚህ ዓይነት ግንኙነት ውስጥ ያሉ ሴቶች በሚስትነታቸውም ሆነ በሰውነታቸው በባሎቻቸውና በፍቅረኞቻቸው የሚሰጣቸው ክብርም ፍቅርም የለም፡፡ እዚህ ላይ ሴቷ የገንዘብ ምንጭ ብቻ ናት፡፡ ከገንዘብም ከወሲብም ጋር በተያያዘ ትበዘበዛለች፡፡ እንደዚህ ያሉ ሴቶች በሥነ ልቦናም በማኅበራዊ ሕይወትም የተሰረቁ ናቸው፡፡
በአንድ በኩል ሴተኛ አዳሪ፣ አልያም የውጭ ዜጐች ቅምጥ ሆነው በሌላ በኩል እንወዳቸዋለን ለሚሏቸው ኢትዮጵያውያን ፍቅረኞቻቸው የገንዘብና የሌሎች ጥቅማጥቅም ምንጭ የሆኑ ሴቶች ምናልባትም እንወዳቸዋለን ከሚሉት ፍቅረኞቻቸው ጋር ‹‹ወደፊት ወልደን ከብደን›› የሚል ራዕይ ይኖራቸዋል፡፡ ይህ ግን እንደ አቶ ዓለሙ እምነት ፍጹም ስህተት ነው፡፡ ‹‹እነዚህ ሴቶች ዛሬ ያልፋል፤ ነገ ይህን ነገር አንድ ቦታ አቁሜ የተሻለ የፍቅር ግንኙነት ይኖረናል ብላ ካመነች ስህተት ነው፤›› በማለት ዋጋ ከማይሰጠው ይበልጡን ሕይወታቸውን አደጋ ላይ በሚጥል ሁኔታ ውስጥ በመግባታቸው ከሚሰማ ወንድ ጋር ዘላቂ ሕይወት ማሰብ መሠረት የሌለው እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡ ይልቁንም በዚህ መልኩ የሰበሰቡት ሀብትና ንብረትን በአጋሮቻቸው ተነጥቀው ከገንዘባቸውም ሳይሆኑ እወደዋለሁ ይወደኛል በሚሉት ሰው የመከዳታቸው እድል ከፍተኛ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡
‹‹ምናልባትም በዚህ ዓይነቱ ግንኙነት ውስጥ ያለች ሴት ትዳር ይዛ ከሆነ ቀደም ብሎ እንዳልተስማማበት፤ የገንዘብ ምንጩ እንዳላደረገው ሁሉ ሴተኛ አዳሪነቷን ወይም የውጭ ዜጋ ቅምጥነቷን በማስረጃ አስደግፎ ወደ ሕግ ሊሔድና ኢላማ ያደረገውን ጥቅም ማግኘት አሳክቶ ሊሔድ ይችላል፡፡››
ኅብረተሰቡን ስለማኅበራዊ እሴቶች ማስተማር፤ የሃይማኖት ተቋማትም ስለግብረገብነት በስፋት በማስተማር የዚህ ዓይነቱን ሁኔታ መግታት ካልተቻለ በቀር የማኅበረሰብ እሴት መሸርሸር የሰው ኃይልን ውጤት አልባ ወደ ማድረግና ወደ ሌሎች ጥፋት እንደሚያመራ አመልክተዋል፡፡ ‹‹የዚህ ዓይነቱ ሁኔታ እየቀጠለ ሥር መስደድ ከጀመረ የትዳር ዋጋ እያጣ ቤተሰብ መመሥረት፣ መውለድና መክበድም

No comments:

Post a Comment