Tuesday, June 24, 2014

ከሕገ-መንግሥቱ በፊት


ትናንት ሰኔ 14 ቀን 2006 ዓ.ም ሰማያዊ ፓርቲ ‹‹ያገባኛል ባይነት እና ጋዜጠኝነት በአምባገነን ሥርዓት ውስጥ›› በሚል ርዕስ እኔን ጋዜጠኛ አናንያ ሶሪ እና ዳዊት ሰለሞንን የውይይት መነሻ እንድናቀርብ በጋበዘን መሰረት በእኔ በኩል ለውይይት መነሻ ሀሰብ ይሆናሉ ብዬ ያቀረብኋቸውን ሶስት ነጥቦች እንዲህ አቅርቤያዋለሁ፡፡

በመጀመሪያ የሰማያዊ ፓርቲ ወጣቶች ጉዳይ ‹‹ያገባኛል ባይነት እና ጋዜጠኝነት በአምባገነን ሥርዓት ውስጥ›› በሚል ርዕሥ የውይይት መነሻ ሀሳብ ከሙያ አጋሮ ቼ ጋር እንዳቀርብ ስለጋበዘኝ በቅድሚያ ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡




የሕገ­መንግሥቱ አንቀጽ 29

ነሐሴ 15 ቀን 1987 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ­መንግሥት ሲጸድቅ የፈረሙበት የወቅቱ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ነበሩ፡፡ ይህ ሕገ­መንግሥት በአንቀጽ 29 (1) እና (2) ላይ ሃሳብን በነጻነት የመገለጽ መብትን በተመለከተ እንዲህ ይላል፡­
‹‹ማናኛውም ሰው ያለማንም ጣልቃ ገብነት የመሰለውን አመለካከት መያዝ ይችላል፡፡ ፣ማንኛውም ሰው ያለማንም ጣልቃ ገብነት ሐሳቡን የመግለጽ ነጻነት አለው፡፡ ይህ ነጻነት በአገር ውስጥም ሆነ ውጪ ወሰን ሳይደረግበት በቃልም ሆነ በጽሑፍ ወይም በሕትመት፣ በሥነ­ጥበብ ወይም በመረጠው በማንኛውም የማሰራጫ ዘዴ፣ በማንኛውም ዓይነት መረጃና ሐሳብ የመሰብሰብ፣ የመቀበልና የማሰራጨት ነጻነቶችን ያካትታል፡፡››
ባለፈው ዓመት መጨረሻ ላይ ከጓደኛዬ አቤል ዓለማየሁ ጋር ‹‹ኢትዮጵያን ማን ይታደጋት?›› በሚል ርዕስ ለንባብ ባበቃነው መጽሐፍ ውስጥ ይህን ሕገ­ መንግሥት አስመልክቶ ዶ/ር ነጋሶን ቃለ መጠይቅ በማድረግ አነጋግረናቸው ነበር፡፡ ከላይ በመግቢያዬ የጠቀስኩት አንቀጽ 29 መከበር አለመከበሩ ከጥያቄዎቼ መካከል አንዱ ነበር፡፡ ዶ/ር ነጋሶም እሳቸው በምላሻቸው እንዲህ አሉ፡­


‹‹እንደ ጥሩ ምሳሌ የጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙን እና የእስክንድር ነጋን ጉዳይ መውሰድ እንችላለን፡፡>> በዚህ አንቀጽ መሠረት፣ ርዕዮት እንደጋዜጠኛ የፈለገችውን ሐሳብ ጽፋ ለየትኛውም ሚዲያ የማቀበል መብት አላት፡፡ ይህ ተጥሶ ‹‹ከሽብርተኛ ድርጅት ጋር ግንኙነት አላት›› ተብሎ ተፈረደባት፡፡ እስክንድር ነጋ በአንድነት ፓርቲ ጽ/ቤታችን ድረስ በሕዝብ ግንኙነት ክፍል ተጋብዞ በመምጣት የቀረበውን ሐሳብ ከተሰብሳቢዎች ጋር ተቀምጬ አዳምጫለሁ፡፡ ሐሳቡን በመግለጹ ‹‹ሽብርተኛ ነው›› ተብሎ ተፈረደበት፡፡ እነ አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ኦልባና ሌሊሳ ‹‹ከአምነስቲ ኢንተርናሽናል ሰዎች ጋር ለምን ተነጋገራችሁ?›› ተብለው ነበር የታሰሩት፡፡ በተጨማሪም በአንድነት ፓርቲ ስር ትታተም የነበረችው የ‹‹ፍኖተ ነጻነት›› ጋዜጣ ያለመታተም ጉዳይ፣ የ‹‹ፍትሕ›› ጋዜጣ መታገድ፣ የ‹‹አዲስ ነገር›› እና የ‹‹አውራምባ ታይምስ›› ጋዜጦች የደረሰባቸውን ችግር እናውቃለን፡፡ አንቀጽ 29 እስከአሁን አልተከበረም፡፡››

እንግዲህ የተከበራችሁ የዚህ ውይይት ተሳታፊዎች፣ ሕገ­መንግሥቱ ላይ ፈርመው ያጸደቁት የቀድሞ ፕሬዚዳንት ሕገ­መንግሥቱ አለመከበሩን ጥቂት ምሳሌዎችን በማቅረብ ተናገርው ነበር፡፡ ይህ የሥርዓቱን ህገ ወጥነት እና አደገኝነት የሚያሳይ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ የጊዜው መንግሥታችን ‹‹ሀገርን የማስተዳድርበት ወርቃማ ሕግ አለ፡፡ ይህ ትልቅ ስኬታችን ነው›› በማለት ዘወትር ሲናገር እንዳደምጠዋለን፡፡ የኢህአዴግ መንግሥት የሕገ­መንግሥቱን አንቀጽ 29 በተለያዩ በርካታ ጊዜያትና በተለያዩ መንገዶች ሲንድ፣ ሲሸራርፍና ሲደፍር፤ ናድኩት፣ ሸራረፍኩና ደፈርኩት አይለንም፡፡ ይልቅ ጥቂት የማይባሉ ጋዜጠኞችን ‹‹ሕገ መንግሥቱን ለመናድ ሲንቀሳቀሱ ... ከአሸባሪ ቡድኖች ጋር በመተባበር የሀገርን መሰረተ ልማቶች በሽብር ለማውደም ሲያሴሩ ...ወዘተ በሚሉ ምክንያቶች ጠርጠሮ በመያዝ በፍርድ ሂደትም በተለያዩ ዓመታት የጽኑ እስራት ቅጣት በይኖባቸዋል፡፡ 

አሁንም በመሰል አካሄዶች ፖሊስ (በሽብርተኝነት ወንጀል) ሶስት ጋዜጠኞች እና ስድስት ጦማሪያን (ብሎገሮች)ን ‹‹ጠጥሬያቸዋለሁ›› በሚል በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ጣቢያ ከታሰሩ ከ56 ቀናት በላይ አልፏቸዋል፡፡ እነዚህ ጋዜጠኞች እና ጦማሪያን ሕገ­መንግሥቱን አክብረው የሚንቀሳቀሱ ነበሩ ብዬ በግሌ አምናለሁ፡፡ ዛሬም ሕገ­መንግሥቱን እና ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ሃሳቦችን አንስተን በጋራ ብንወያይ ወሳኝ ጉዳይ ይመስለኛል፡፡ መንግሥት ሕገ­መንግሥቱ በመናድ ብሎ ጋዜጠኞችን ፖለቲከኞችንና ዜጎችን በሕግ ተጠያቂ እንደሚያደርግ ሁሉ እሱም የሕገ­መንግሥቱን ድንጋጌዎች ሲንድ፣ ሲሸራርፍና ሲደፍር በሕግ እንዴት ተጠያቂ ማድረግ ይቻላል? በሚለው ላይ እንነጋገር እና የመፍትሔ ሀሳቦች ይንሸራሸሩ፡፡




ከሕገ­መንግሥቱ በፊት

ኢህአዴግ 1983 ዓ.ም ላይ የደርግ ሥርዓትን ከገረሰ በኋላ ነጻ ፕሬስ ማወጁ ብዙዎቻችንን የሚያስማማ እና ሊመሰገንበት የሚገባ ትልቅ እርምጃ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ነገር ግን፣ ሥርዓቱ ይህንን በማድረጉ ከሰማይ መና እንዳወረደ ተደርጎ መቆጠር አለበት አልልም፡፡ መንግሥት በተለያዩ ጊዜያት፣ በተለይ እራሱ ጠቅልሎ በያዛቸው እና እንደፈለገ በሚዘውራቸው ሚዲያዎች ነጻ ፕሬስ ማወጅ መቻሉን ከሚጠበቀው በላይ በማጋነን ለፕሮፖጋንዳ ፍጆታነት ሲጠቀምበት ተመልክተናል፡፡ ኢህአዴግ በትረ­ሥልጣን ባይይዝ ኖሮ ኢትዮጵያ ውስጥ ነጻ ፕሬስ ፈጽሞ አይታወጅም ብሎ መደምደምም ከባድ ነው፡፡ (እንዲህ ብለው የሚያስቡ ስላሉ ነው) በዚያን ጊዜ ከዓለም ነባራዊ ሁኔታ ጋር ለመሄድ ኢህአዴግ ነጻ ፕሬስን ማወጁ የውዴታ ግዴታውም ነበር ከልቡ ቢያምንበትም ባያምንበትም፡፡

ከነጻ ፕሬሱ እወጃ በኋላ ባሉት ዓመታትም፣ እስከአሁን ድረስ የኢትዮጵያ ነጻ ፕሬስ በምን አይነት አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሲዳክር መጓዙን መናገር ለቀባሪ እንደማርዳት ስለሚሆን አልፈዋለሁ፡፡ አንድ ጉዳይ ግን በውስጤ ብዙ ጊዜ ይብሰለሰላል፡፡ እራሴንም ደጋግሜ ጠይቄ ለራሴ መልስ አግኝቼለታለሁ፡፡ የኢሕአዴግ መንግሥት የሕጎች ሁሉ የበላይ ሕገ መንግሥቱ ብቻ መሆኑን ደጋግሞ ነግሮናል፡፡ ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ከሕገ­መንግሥቱ በፊት ቀዳሚ መሆኑ ይሰማኛል፡፡ ይህንን የምለው፣ ተፈጥሮ የሰውን ልጅ በነጻነት እንዲያስብ፣ ሐሳቡን ሐላፊነት በተሞላው መልኩ እንዲናገር፣ እንዲጽፍ፣ በተለያዩ ጥበባቶችና የመግባቢያ መንገዶች እንዲያስተላልፍ እና እንዲቀበል ቀድማ ለግሳዋለች፡፡ ይህንን የላቀ የተፈጥሮ ሕግ ከሕገ­መንግሥት ጋር ተሰናስሎ በሕግ ማዕቀፍ መደገፉ ጥቅሙ የላቀ መሆኑ አከራካሪ አይመስለኝም፡፡

በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ዓይነት አምባገነን ሥርዓቶችን ያየች ሀገር ቀላል የማይባሉ ዜጎች ተፈጥሯዊውንም ሆነ ሕገ­መንግሥታዊ የማሰብ፣ የመናገር፣ የመጻፍ ...ወዘተ መብቶቻቸው ተሸብቦ በፍርሃት ቆፈን ውስጥ መውደቃቸውን አምናለሁ፡፡ ይህም ሥርዓታቱ (ደርግ የለየለት፣ ኢህአዴግ ደግሞ ዴሚክራሲያዊ ካባ የደረበ አንባገነን ነው) ለሥልጣናቸው ማቆያ እና ማራዘሚያ ሲሉ ከእነሱ ሃሳብ በተቃራኒው በሚያስቡ እና በድፍረት በሚናገሩ፣ በሚጽፉ ...ዜጎቻቸው ላይ በሚወስዷቸው ኢ­ፍትሃዊ የግድያ፣ የድብደባ፣ የእስር፣ የእንግልት፣ የስደት ...እርምጃዎች በዋነኝነት የሚመጣ ነው፡፡ አፋኝ የሆነው የጸረ­ሽብርተኝነት አዋጁም ኢትዮጵያኖችን ተፈጥሮ የለገሰቻቸውን የማሰብ፣ የመጻፍ፣ የመናገር ...መብቶች በእጅጉ የሚጨቁን ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ በመሆኑም ኃላፊነት በተሞላው መንገድ ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን በሕግ ማዕቀፍ ውስጥ አስገብቶ የማክበር እና የማስከበር ግዴታን እንዴት እንወጣው? በሚለው ላይ

 ከሕገ-መንግሥቱ በፊት 
ብንወያይበት መልካም ነው ብዬ አስባለሁ፡፡




የእስረኞች አያያዝ እና ሰብዓዊ መብቶች

በሕገ­መንግሥቱ አንቀጽ 18 (1) ላይ ‹‹ማንኛውም ሰው ጭካኔ ከተሞላበት፣ ኢ­ሰብዓዊ ከሆነ ወይም ክብሩን ከሚያዋርድ አያያዝ ወይም ቅጣት የመጠበቅ መብት አለው›› ይላል፡፡ ይህ ግን በተለያዩ ጊዜያት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ በግልጽ እየተጣሰ እንደሚገኝ እየደመጥን ያለነው፡፡ በዚያ ጭካኔ የተሞላበት ድርጊት ይፈጸማል፡፡ ‹‹እመኑ›› ወይም ‹‹በሌላ ሰው ላይ መስክሩ›› ተብሎ ቶርች ይደረጋል፡፡ ዜጎች ይደበደባሉ፣ ውስጥ እግራቸው ይገረፋል፣ ቀዝቃዛ ውሃ ይደፋባቸዋል፡፡ ‹‹ወፌ ላላ›› የተባለ አውጫጭኝ ግርፍ ሰዎች እንደሚገረፉ ይነገራል፡፡ ይሄንን ጋዜጠኛ አና ጦማሪ በፍቃዱ ሐይሉ፣ ጦማሪያኑ አቤል ዋበላ እና አጥናፍ ድብደባ እና ጥፊ የመብት ጥሰት እንደደረሰባቸው ለፍርድ ቤት ተናግረዋል፡፡ እኔም ለጥቂት ቀናት ማዕከላዊ ታሰሬ በነበረበት ጊዜ ከብዙ ታሳሪዎች ድርጊቱ እንደሚፈጸም አረጋግጫለሁ፡፡ እኔ ታስሬበት በነበረበት ‹‹8›› ቁጥር ውስጥ ከጎንደር የመጣ ብርሃኑ የተባለ ሰው በድብደባ ብዛት እያነከሰ ነበር የሚሄደው፡፡ ከደቡብ ሱዳን በሽብር ጉዳይ ተጠርጥረው ከተያዙት መካከል ከአንዱ የቀድሞ የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት (አቶ ኦኬሎ) በስተቀር መደብደባቸውን አረጋግጠውልኛል፡፡ የተደበበደቡትን የአካላቸውን ክፍል አሳይተውኛል፡፡ ለአራት ቀናት ያህል እንዲቆም የተቀጣ ወጣትም የደረሰበትን በመረረ መልኩ ነግሮኛል፡፡ በማንኛውም መንገድ ተጠርጥረው የተያዙ ዜጎች ሰብዓዊ መብቶቻቸው ሲጣስ ‹‹ያገባናል፣ ድርጊቱ ተገቢ አይደለም፡፡ ይህንን የሚፈጽሙ ግለሰቦች እና አካላት በሕግ መጠየቅ አለባቸው›› ብለን በድፍረት መናገር፣ የሚመለከተውን አካል መጠየቅና ድምጻችንን በተለያየ መንገድ ማሰማት ይገባናል፣ ለተግባራዊነቱም መንቀሳቀስ ይጠበቅብናል፡፡

በመጨረሻም በጣም በማከብራቸው ምሁር ፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማሪያም ሰኔ 13 ቀን 2006 ዓ.ም በነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ላይ ‹‹ጋዜጠኞችንና ጦማሪያንን ማን ይፈራቸዋል?›› በሚል ርዕስ ለንባብ ካቀረቡት ጽሁፍ ውስጥ የማረከኝን ሀሳብ በመውሰድ የውይይት መነሻ ሃሳቤን እቋጫለሁ፡፡
‹‹ ...ለእኔም ነጻ ጋዜጠኞች እና ጦማሪያን የሌሉበት ገዥ አካል ከሚኖር ወይም ደግሞ ገዥ አካል በሌለበት ነጻ ጋዜጠኞች እና ጦማሪያን ብቻ ከሚኖሩ የትኛው የተሻለ የሚል ምርጫ ቢቀርብልኝ የኋለኛውን ለመምረጥ ለሰከንድ እንኳ ጥርጣሬ አይኖረኝም፡፡ ከሁሉም በላይ ለዓላማ በጽናት የቆምኩ፣ ለምሰራው ትክክለኛ ሥራ ሁሉ ኩራት የሚሰማኝ፣ ላመንኩበት ዓላማ ከልብ እና በወኔ የቆምኩ፣ ዓላማዬን ለማስፈጸም በከባድ እርምጃ ወደፊት የምገሰግስ፣ ላልሰራሁት ወንጀል ይቅርታን የማልጠይቅ፣ በምሰራው ሥራ ሁሉ የማላፍር፣ ቆራጥ እና የማያወላውል ባህሪን የተላበስኩ 

የኢትዮጵያ ጦማሪ ነኝ፡፡››

ኃይል ለነጻ ጋዜጠኞችና የኢትዮጵያ ጦማሪያን! 

No comments:

Post a Comment