Thursday, November 8, 2012

ኢህአዴግ ስንት ቦታ ሊሰነጠቅ ይችላል?



  (ከተመስገን ደሳለኝ)

ብርዱ የጥቅምት ነው፤ አጥንት ድረስ ዘልቆ የሚያንቀጠቅጥ ኃይለኛ ቅዝቃዜ፡፡ አዲስ አበባ ገና ከእንቅልፏ
በመንቃት ላይ ነች፡፡ ለስራ የቸኮሉ መንገደኞች ትራንስፖርት ፍለጋ ወዲያ ወዲህ ይካለባሉ፡፡ ማክሰኞ
ጥቅምት 7 ቀን 2005 ዓ.ም. ከጠዋቱ 12 ሰዓት ከ50 ደቂቃ ላይ ብስራተ ገብርኤል አደባባይ ‹‹መገናኛ
ራዲዮ›› በያዙ የትራፊክ ፖሊስ አባላት በቁጥጥር ስር ዋለ፡፡ የትራፊክ ፖሊሶቹ ስራ የበዛባቸው ይመስላሉ፡፡
12 ሰዓት ከ55 ደቂቃ ሲል በሁለት የሞተር ብስክሌት በተፈናጠጡ የትራፊክ ፖሊሶች ፊት አውራሪነት
አንዲት ሳይረን የተገጠመላት የፖሊስ ታርጋ የለጠፈች መኪና የ‹‹መንገድ ልቀቁልኝ›› ጩኸቷን እያንባረቀች
አቋርጣ በማለፍ ወደ ሳር ቤት አቅጣጫ ከነፈች፡፡ ሶስት ‹‹ቪኤት›› መኪና ሰለሱ፡፡ ሌላ ባለሳይረን መኪናም
ከኋላ እየተከተለች ነው፡፡ ሁሉም መኪኖች በከባድ ፍጥነት ነው የሚበሩት፡፡ ሳር ቤት ያለው የፑሽኪን
አደባባይም ተመሳሳይ ቁጥር ባላቸው የትራፊክ ፖሊሶች ተጨናንቋል፡፡ ሜክሲኮ አደባባይ፣ አምባሳደር፣ ፍልውሃ፣ ገብርኤል መሳለሚያ…

ቤተ-መንግስቱ የአጀቡ መድረሻ ቦታ ነው፡፡
አጀቡ አዲሱን ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝን ከመኖሪያ ቤታቸው ወደ ስራ ቦታቸው ለማድረስ ነው፡፡ ይኸው ትዕይንት ከምሽቱ
ሶስት ሰዓት ላይ ይደገማል፡፡ ቅደም ተከተሉ ተገልብጦ፤ ከቤተ-መንግስት… ብስራተ ገብርኤል፤ የአደጋ ማስጠንቀቂያ ድምጽ፡፡
ሀገሪቱ በማን ነው የምትመራው?
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝ በየትኛውም ሀገር ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ለሰላሳ አንድ ቀናት ከመኖሪያ ቤታቸው ወደ
ቤተ-መንግስት፤ ከቤተ-መንግስት ወደ መኖሪያ ቤታቸው እየተመላለሱ ለመስራት ተገደው መቆየታቸው የሀገር ውስጥንም ሆነ የአለም
አቀፉን ሚዲያ ትኩረት የሳበ ጉዳይ ሆኖ አልፏል፡፡ የዓለም አቀፍ የሚዲያ ተቋማት ይህንን ጉዳይ አጀንዳ ከማድረጉም በላይ የናይጄሪያ
ቴሌቪዥን ‹‹ቤተ-መንግስቱን ልቀቂ-አለቅም›› በሚለው የሀገራችን ፖለቲካዊ ድራማ ላይ በማፌዝ አንድ ፕሮግራም እስከማስተላለፍ
ደርሷል፡፡ አዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ለዚህ አይነት እንግልት የተዳረጉት የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ቤተ-
መንግስቱ ውስጥ የሚገኘውን የጠቅላይ ሚንስትር መኖሪያ ቤት ለመልቀቅ ፍቃደኛ ሆነው ባለመገኘታቸው ነው፡፡ የሴቲቱ መከራከሪያ
ሃሳብ ‹‹በቅያሬ ሊሰጠኝ የታሰበው ቤት ለደህንነቴ ያሰጋል›› የሚል ነበር፡፡ በእርግጥ ይህ መከራከሪያ ውሃ አያነሳም፡፡ በየትኛውም
መመዘኛ ቢታይም ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ ምን አልባት ይህ መከራከሪያ አግባብ ሊሆን ይችል የነበረው ‹‹ለቅያሪ የተሰጠኝ ቤት
ለደህንነቴ ስለሚያሰጋ አስተማማኝ ቤት ይፈለግልኝ›› ብለው ለሚመለከተው ክፍል በአቤቱታ መልክ ቢያቀርቡ ነበር፡፡ በተቀረ እንዲህ
እንደሰማነው ‹‹ግዛቴን አልለቅም!›› ብሎ ማመፁ የፓርቲያቸው ጤና መታወክን ነው ሊያመላክት የሚችለው፡፡ አሊያም የአዜብን
መከራከሪያ ሌሎች የግንባሩ የአመራር አባላቶች ደፍረው ሊነግሩን ያልሞከሩትን በስርዓቱ ላይ የተከሰተውን የ‹‹ማዕከላዊ አስተዳደር››
ድክመት ወይም በሌላ አማርኛ በኢህአዴግ ውስጥ መከፋፈል ስለመፈጠሩ በገደምዳሜ መልዕክት እያስተላለፈ ነው ወደሚል
መደምደሚያ የሚያደርስ አድርገን ልንወስደው እንችላለን፡፡ ምክንያቱም በዚህ ጉዳይ ላይ ሙግት የሚያነሱ ሰዎች የስነ-ሀሳብ ክርክራቸው
የሚያርፈው በሁለት ጥያቄዎች ላይ ነውና፡፡ በአሁኑ ወቅት ለሀገሪቱ ወሳኝ የሆነው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ደህንነት ነው? ወይስ የቀድሞ
ጠቅላይ ሚኒስትር ባለቤት ደህንነት? የእነዚህ ጥያቄዎች መልስም የሀገሪቱን መረጋጋት ወይም የሹመቱን ‹‹ስማዊነት›› ይነግሩናል፡፡
አይበለውና! ጠንካራ ጥበቃ ከሚደረግለት ‹‹የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚንስትር መኖሪያ ቤት›› ውጪ ለተጠቀሱት ቀናት ያህል ለመኖር
የተገደዱት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ከቤት ወደ ቢሮ ሲሄዱ፣ አሊያም ከቢሮ ወደ ቤት ሲመለሱ በ1987 ዓ.ም በሆስኒ ሙባረክ
ላይ የተሞከረው ግድያ አይነት አደጋ ቢያጋጥማቸው ኖሮ ኃላፊነቱን የሚወስደው ማን ነበር? አደጋውን ተከትሎ የሚፈጠሩ ቀውሶችስ ምን
ሊያስከትሉ ይችሉ ነበር? ይህንን ችግር በህግ አግባብ መፍታት የነበረበትስ ማነው? የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ወይስ ከጠቅላይ
ሚኒስትሩ ጀርባ ባለው ወንበር ላይ የተቀመጡ ‹‹ኃያላኑ›› አንጋፋ ታጋዮች?
በእነዛ ሁሉ ቀናት በቤተ-መንግስቱ ለጥበቃ ስራ የተመደበው እስከ አፍንጫው የታጠቀ ሰራዊት ታዛዥነቱ ለማን ነበር? እንደፋብሪካ
ወዛደር በሰዓት ገብተው በሰዓት ለሚወጡት ጠቅላይ ሚኒስትር? ወይስ በውሎና በአዳራቸው ከሰራዊቱ ለማይለዩት አዜብ መስፍን?...
አሁንም አይበለውና! ሴቲቱ ለሃያ አንድ አመታት የቀኝ እጃቸው ሆኖ የቆየውን ሰራዊት ‹‹በለው በለውና፣ አሳጣው መድረሻ!›› የሚል
ቀጭን ትዕዛዝ ቢያስተላልፉለት ኖሮ ምንድር ነበር የሚከተለው? ደህና! ከእነዚህ ሁኔታዎች ተነስቶም ሀገሪቱ የምትመራው በማን ነው?
ቃለ-መሀላ ፈፅመው ስልጣን በያዙት ኃይለማርያም ደሳለኝ ወይስ የህወሓት/ኢህአዴግ የአመራር አባልና የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር
ባለቤት በሆኑት አዜብ መስፍን? የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል፡፡ በእርግጥ የዚህን መልስ ለማግኘት ጥቂት ጊዜ መታገስን ይጠይቃል፡፡
በኢትዮጵያ መንግስት ከወዴት አለ?
      ተመስገን ደሳለኝየቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር በሀገሪቱ ላይ ‹‹ወጥ አምባገነናዊ ስርዓት›› አስፍነው የነበረ ቢሆንም በዘመነ መንግስታቸው ቢያንስ ማዕከላዊ
መንግስት እና የስልጣን ተዋረዱን የጠበቁ የተለያዩ ተቋማት (ምንም እንኳን ተጠሪነታቸው ከህገ-መንግስቱ እና ከተቋቋሙበት አዋጆች
ይልቅ ለእርሳቸው ቢሆንም) በመኖራቸው ‹‹መንግስት›› ተብሎ ሊጠራ የሚችል አስተዳደር መኖሩ ላይ የሚነሳ ጥያቄ አልነበረም፡፡
    ነገር ግን የፓርቲ እና የመንግስትን ስልጣን ጠቅልለው ይዘው የነበሩት የአቶ መለስ ህይወት ማለፍን ተከትሎ ‹‹ማዕከላዊ መንግስት››
እየተዳከመ እንደሆነ ወይም ኢህአዴግ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሊሰነጠቅ እንደሚችል ፍንጮች እየታዩ ነው፡፡ የዚህ ምክንያት ደግሞ በራሱ
በድርጅቱ ውስጥ የተለያየ ፍላጎት ያላቸው ቡድኖች የተለያየ ሃሳብ ይዘው ማቆጥቆጣቸው ነው፡፡ በእርግጥ በአምባገነናዊ ስርዓት ውስጥ
እንዲህ ዓይነት የስልጣን ክፍተት (Power Vacuum) በሚኖርበት ጊዜ የተለያዩ ቡድኖች መፈጠራቸው የሚጠበቅ ነው፡፡ በኢትዮጵያ
የተከሰተውም ይኸው ነው፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ሚዲያውን የያዘው ቡድን ማዕከላዊ መንግስት ጠንካራ ለመሆኑ ምስክር የሚመስሉ
እርምጃዎችን ወስዷል (አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትር መምረጥ፣ ለከፍተኛ የጦር መኮንኖች ሹመት መስጠት፣ አምባሳደሮችን መመደብ፣
ሽግሽጉን ተከትሎ የተፈጠረውን ክፍተት መሙላት ለምሳሌ፡- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርን መምረጥ) ይህ ኃይል በዚህ እርምጃው መለስ
ቢሞቱም መንግስት በነበረበት የሚቀጥል እንዲመስል ማድረግ ችሎ ነበር፡፡
   በአናቱም የአቶ መለስ ህይወት ማለፍ በይፋ ከመነገሩ ጥቂት ቀናት አስቀድሞ የስርዓቱ ‹‹መፈንሳዊ አባት›› እንደሆኑ የሚነገርላቸው
አቦይ ስብሓት ነጋ አቶ መለስ አንድ ሰው መሆናቸውን፣ የእሳቸው ማለፍም የሚያመጣው ነገር ያለመኖሩን ለመግለፅ ‹‹መለስ መጣ፣ መለስ
ሄደ፤ ፋጡማ መጣች፣ ፋጡማ ሄደች፤ በቀለ መጣ፣ በቀለ ሄደ…›› ሲሉ ለአሜሪካ ድምጽ የሰጡት ቃለ መጠይቅም ይህንኑ የሚያጠናክር
ነበረ፡፡ ነገር ግን የአቶ መለስን ማለፍ መንግስት ይፋ ካደረገ በኋላ የተከተሉት ነገሮች መለስ ለኢህአዴግ መራሹ መንግስት እንደ አንድ መሪ
(ግለሰብ) ብቻ እንደማይታዩ የሚያረጋገጥ ሆኖ አልፏል፡፡ መለስ ለሀገሪቱ ሁሉም ነገር መሆናቸውን በመንግስት መገናኛ ብዙሃን ለበርካታ
ቀናት ደጋግመው የነገሩን ጓዶቻቸው ራሳቸው ናቸው፡፡ በሚቀጥሉት አስር እና ሃያ አመታትም ሀገሪቱ የምትመራው በመለስ ራዕይ እንጂ
ከአለም አቀፍ ነባራዊ ጉዳዮች እና ከወቅታዊ ሁኔታዎች ጋር እየተገናዘበ በሚቀረፅ ፖሊሲ እና በሚነደፍ እቅድ እንዳልሆነም ጨምረው
ነግረውናል፡፡ መቼም ይህ ፕሮፓጋንዳ ሲፋቅ የሚገኘው እውነት ‹‹ለመጪዎቹ አስርና ሃያ ዓመታት ኢህአዴግ በመለስ ራዕይ ሳይበታተን
በስልጣኑ ይቀጥላል›› የሚል ሊሆን ይችላል፡፡
በአጠቃላይ ግን በሀገሪቱ ላይ ኃላፊነት የሚወስድ ማዕከላዊ መንግስት ያለመኖሩን የሚያሳየን ወይም ለክርክር የሚጋብዘን፤ አዲስ
የተመረጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ‹‹ጥርስ የሌለው አንበሳ›› ተደርገው መሰራታቸው ነው፡፡ በእርግጥም ኃይለማርያም ደሳለኝ ከዚህ ቀደም
የደኢህዴን የአመራር አባላትን ያለፓርቲው ውሳኔ ከኃላፊነታቸው ሲያነሱ ‹‹ከበላይ ታዝዤ ነው›› ይሉ በነበረበት መንፈስ ውስጥ
ለመሆናቸው ዋነኛ ማሳያ ከሆኑት አጋጣሚዎች አንዱ ወ/ሮ አዜብ ከህግ ይልቅ ፖለቲካዊ ጉልበትን ሲጠቀሙ የፈየዱት ነገር አለመኖሩ
ነው፡፡ (በነገራችን ላይ ምክትል ጠ/ሚንስትሩም መወሰን ያለባቸውን ጉዳዮች ከመወሰናቸው በፊት ‹‹አቶ አዲሱን ላማክር›› የሚል ነገር
ያበዛሉ ሲሉ በቅርበት የሚያውቋቸው ይተቿቸዋል) በእርግጥ አዜብ ቤተ-መንግስቱን አልለቅም ማለታቸው ያሳጣው መንግስትን ብቻ
አይደለም፤ በአቶ መለስ ስርዓተ ቀብር ዕለት ወይዘሮዋ እራሳቸው ‹‹የመለስ ራዕይ ካልተበረዘ እና ካልተሸራረፈ …›› ሲሉ
እንደሚያስፈፅሙ የገቡለትንም ቃል ጭምር ነው፡፡ ምክንያቱም አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ስልጣን የያዙት በፓርቲው ህገ-ደንብ መሰረት
ነው፡፡ ህገ-ደንብ ደግሞ የመለስ ራዕይ ውስጥ የሚካተት ነው፡፡ ከዚህ ስንነሳ የምንደርስበት እውነታ ኢህአዴግ ውስጥ መደማመጥ እየራቀ
መሆኑን ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ ‹‹የመለስ ራዕይ›› የሚል ስያሜ የተሰጠውን የኃይል ማሰባሰቢያ ባንዲራ እንኳ በህብረት ማውለብለብ
እየተሳነው ነው፡፡
   የሆነ ሆኖ በግንባሩ ውስጥ የፖለቲካ ቅሬታ ያላቸው ያውም ‹‹አደገኛ›› ሰዎች ለመኖራቸው ምልክቶች መታየታቸው አጠያያቂ
አይደለም፡፡ ለዚህ ዕውነታ መከራከሪያ ተደርግው ከሚቀርቡት ማሳያዎች ውስጥ አንዱ በዚህ የእምቢተኝነት እና የስርዓት አልበኝነት
ተግባራቸው የፓርቲው ማዕከላዊ አመራር መሰባበሩን በተዘዋዋሪ ያሳወቁን አዜብ መስፍን የፓርቲው የስራ አስፈፃሚ አባል መሆናቸው
ነው፡፡ ምን አልባትም በሀገሪቱ ፖለቲካ ላይ ምንም አይነት ተሳትፎ ያልነበራቸው፤ ወይም ‹‹የኢትዮጵያ ሰራተኞች ፓርቲ/ኢሰፓ››
የአመራር አባል ያልነበሩት የቀድሞ ፕሬዘዳንት የመንግስቱ ኃ/ማርያም ባለቤት ይህንን ስህተት ቢፈጽሙ ኖሮ ጉዳዩን ከስርዓቱ እና
ከፖለቲካው ጋር በቀጥታ ማገናኘቱ አስቸጋሪ ይሆን ነበር፡፡ ነገር ግን ድርጊቱን የፈፀሙት ወ/ሮ አዜብ፣ ታግለው ለስልጣን የበቁና ገዥውን
ፓርቲ ወክለው ፓርላማ የገቡ ከመሆናቸውም በላይ የገዢው ፓርቲ የስራ አስፈፃሚ አባል ናቸው፡፡ ስለዚህም የስልጣን ተዋረዱም ሆነ
ውስጣዊ መረጋጋቱ በነበረበት ያለ መሆኑ በተነገረለት ፓርቲ ውስጥ የዚህን ያህል ከፓርቲያቸውና ከመንግስት ትዕዛዝ ሊያፈነግጡ
የሚችሉበት አሰራርም ሆነ ደንብ አይኖርም፡፡
በአጠቃላይ ‹‹በግንባሩ ውስጥ ልዩነት ተከስቷል›› የሚለውን ጥርጣሬ የሚያሰፋው መንግስትም ሆነ ፓርቲያቸው ሴቲቱን እንደመንግስት
ለማስገደድ ሲሞክር አለመታየቱም ጭምር ነው፡፡ ሲሞን አሊሶን የተባሉ ፀሀፊ ‹‹ዴይሊ ማቭሪክ›› በተባለ ድረ-ገፅ ላይ ‹‹Grieving
widow stalls smooth transition›› በሚል ርዕስ ባስነበቡት ፅሁፍ ያነጋገሯቸው አንድ ኢትዮጵያዊ የፖለቲካ ተንታኝ ጉዳዩን
በግልፅ ቋንቋ ሲያስቀምጡት ‹‹ሴቲዬይቱ የመለስ ባለቤት ብቻ ሳትሆን ባለቤቷ ባነበሩት የከፋ አገዛዝ ሁለተኛዋ ፈላጭ ቆራጭ ናቸው፡፡›› ብለዋል፡፡ ተንታኙ ‹‹በቅርብ የሚያውቋቸው እንደሚሉት ሴትየዋ አስቸጋሪ ባህሪ ያላቸውና ከቀድሞ ባለቤታቸው የባሰ አምባገነን››
መሆናቸውን አስረግጠው ይናገራሉ፡፡
ይህ ሁሉ ከሆነ በኋላ የማታ ማታ ወ/ሮ አዜብ ምክንያቱ ባልተገለፀ ሁኔታ ቤተ-መንግስቱን መልቀቃቸው ተነግሯል፡፡ ሆኖም ላለፉት ሰላሳ
አንድ ቀናት በእምቢተኝነት በመፅናታቸው የተበላሸውን የድርጅቱን ፖለቲካ መጠገን ከቶም አይቻላቸውም፡፡ የጎደፈውን ‹‹ደካማ
አመራር›› ትችት ማጠብ ያዳግታል፡፡ የአመራሩን መከፋፈልም እንዲሁ መሸፋፈን አይቻልም፡፡ ጉዳዩ አንዴ የፈሰሰ ውሃ ሆኖአልና፡፡
ወ/ሮ አዜብ የተማመኑበት የፖለቲካ እና የታጠቀ ኃይል ሳይኖር ከመንግስትም ሆነ ከድርጅታቸው ፍላጎት እና ትዕዛዝ በዚህ ደረጃ
ያፈነግጣሉ ብሎ መቀበሉ ይከብዳል፡፡ ምንአልባትም አዜብ የተማመኑት በታጠቀው ኃይል ሊሆን ይችላል ብሎ መገመት ይቻላል፡፡
በተለይ በቤተ-መንግስቱ ያለውን ሰራዊት፡፡ ከዚህ በመነሳት በሃሜት ኮሪደሮች ሲነገር የነበረውን ‹‹አቶ መለስን እና ቤተሰቦቻቸውን
የሚጠብቀው ሰራዊት አባላት በሙሉ የአቶ መለስ የትውልድ ቦታ የሆነው የአድዋ ተወላጆች ናቸው›› የሚለውን ለማመን እንገደዳለን፡፡
ይህ እውነት ከሆነ ደግሞ ያ ኃይል ታማኝነቱ እና ተጠሪነቱ ለህገ-መንግስቱ ሳይሆን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ መሆኑ አይቀርም፡፡ እናም ይህ
ሠራዊት ለቤተሰቦቻቸው ‹‹ጥላ ከለላ›› የመሆን ዝንባሌ የለውም ማለት ይከብዳል፡፡ የአዜብ ከመንግስት እና ከህግ በላይ መሆንም በዚሁ
ኃይል መተማመን ያመጣው ስሜት ይመስለኛል፡፡ እዚህ ጋ የሚታየው ተጨማሪ አደጋ አዜብ በብዙ ድርድር ቤተ-መንግስቱን ቢለቁም፤
‹‹ጋሻ›› ያደረጉት ሰራዊት አሁንም በነበረበት ግቢ ውስጥ መሆኑ ነው፡፡ ይህን ሰራዊት ሊያዘው የሚችለው ተቋም የመጨረሻ ተጠሪነቱ
ለጠቅላይ ሚንስትሩ መሆኑ ግልፅ ቢሆንም ይህ ያለመፈፀሙን እያየን ነው፡፡ ከሰሞኑ ሁኔታዎች አኳያ ተነስተንም ሠራዊቱ በተሰበረ
የስልጣን ተዋረድ ስር ውሏል የሚል እምነት ላይ ከደረስን ለአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ታማኝ ይሆናል ማለቱ አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ የዚህ
ግልባጭ የሰራዊቱ ታማኝነት ለሴቲቱ እንደሆነ ይቀጥላል የሚል ነው፡፡ ይህ ደግሞ በሴቲቱና ከጀርባቸው ባለው ቡድን እና የመንግስትን
ኃይል ይዣለሁ በሚለው መካከል አንዳንድ አለመግባባቶች ከተፈጠሩ በማንኛውም ሰዓት መፈንቅለ መንግስት አያደርግም ብሎ ማሰብ
አይቻልም፡፡ ይህን መላምት አንዳንድ ፀሀፊዎችም ደጋግመው ይጠቅሱታል፡፡
መቼም እየተነጋገርን ያለው በቤተ-መንግስቱ ስላለው ሰራዊት ብቻ እንዳልሆነ እንግባባለን ብዬ አስባለሁ፡፡ ምክንያቱም ያንን ሠራዊት
በትውልድ መንደር የተሳሰረ ነው ብለን ካመንን፣ የትስስሩ ገመድ የት ሊደርስ እንደሚችል መገመት አያቅትምና ነው፡፡ በተጨማሪም አዜብ
መስፍን የሀገሪቱ ታላቅ የቢዝነስ ተቋም የሆነው ‹‹ኤፈርት›› ኃላፊ መሆናቸው መዘንጋት የለበትም፡፡ የኤፈርትን ገቢና ወጪ ደግሞ እንኳን
ኦዲተር ኢትዮጵያም እንደማታውቀው ለዓመታት ሲነገር የነበረ የአደባባይ ጉዳይ ነው፡፡ እናስ! ገንዘብ ካለ…  (በነገራችን ላይ በቅርብ ጊዜ
ውስጥ ህውሓት ውስጥ ልዩነት የሚከሰት ከሆነ ከኤፈርት ጋ መያያዙ አይቀሬ ነው፡፡ ባለፀጋ ጄነራሎችም የልዩነቱ ዋነኛ ተዋናይ ሲሆኑ
ማየታችን እንዲሁ አይቀሬ ነው) በእርግጥ ‹‹ቡድንተኛ›› በበዛበት ስርዓት ውስጥ የመፈንቅለ መንግስት አደጋ የሚያሰጋው ከአንድ
አቅጣጫ ብቻ አይደለም፡፡ ከሌላም ካልታሰበ እና ካልተጠረጠረ ቦታም የመነሳት ታሪካዊ ዳራ አለው፡፡ በዚህ ወቅትስ እነማን በአሳቻ ቦታ
ምን እየሰሩ እንደሆነ ማን ያውቃል? መቼም ጠቅላይ ሚንስትሩ ያውቃሉ የሚል ቧልተኛ እንደማይኖር አምናለሁ፡፡
እናም በደምሳሳው ከዚህ አኳያ ተነስተን ሁለት ፖለቲካዊ አሳሳቢ አደጋዎችን ልንገምት እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው አዜብ የተማመኑበት
ኃይል ከመንግስት የበረታ ጡንቻ ያለው መሆኑን ነው፡፡ ይህ ባይሆን ኖሮ መንግስት ‹‹ህግ እና ስርዓት››ን በኃይል ለማስከበር ይህንን ያህል
ጊዜ ሊወስድበት አይችልም ነበር፡፡ ጉዳዩን ይበልጥ ግልፅ ለማድረግ የጁነዲን ሳዶን ዕጣ ፈንታ ለንጽጽር በምሳሌነት ማቅረብ እንችላለን፡፡
የሆነው እንዲህ ነው፣ የኦህዴድ/ኢህአዴግ የአመራር አባልና የሲቪል ሰርቪስ ሚንስትሩ ጁነዲን ባለቤት ከሽብርተኝነት ጋር በተያያዘ
በፌደራል ፖሊስ ተይዘው ይታሰራሉ፤ ጁነዲንም ይህንን ጉዳይ በመቃወም ‹‹ባለቤቴ ንፁህ ነች›› ሲሉ በጋዜጣ ላይ ያለቃቅሳሉ፡፡ በዚህ
የተከፉት ጓዶቻቸውም ‹‹የፓርቲውን ገፅታ አበላሸ›› ይሉና ለግምገማ ያቀርቧቸዋል፡፡ በግምገማው ላይ በተደረገባቸው ጫናና
በቀረበባቸው ውግዘት ‹‹ሂሴን ውጫለሁ›› ቢሉም ከፓርቲው አመራርነት ከመሻር አላመለጡም፡፡ እንግዲህ ንፅፅሩ ‹‹ቤተ-መንግስቱን
አለቅም›› ካሉት አዜብ መስፍን ጋር ነው፡፡
በአናቱም ከሴቲቱ እምቢታ ጀርባ ያለው ፖለቲካዊ አንድምታ ሲተነተን ‹‹የኃይለማሪያምን ሹመት አልቀበልም›› የሚል ሊሆን ይችላል፡፡
አንድ ለግንባሩ ቅርበት ያላቸው ግለሰብ ያጫወቱኝም ይህንኑ የሚያጠናክር ነው፡፡ የግንባሩ ሊቀመንበር እና ምክትላቸው በተመረጡበት
ስብሰባ ላይ አዜብ ከምርጫው በፊት አስተያየት አለኝ ይሉና ዕድሉ ሲሰጣቸው ‹‹አዲስ ከሚመረጡት አመራሮች መሀል አንዲት ሴት እና
ነባር አባል መካተት አለባት›› የሚል ሃሳብ ያቀርባሉ፡፡ ነገር ግን ይህ ሃሳባቸው ወዲያውኑ በተቃውሞ ወድቅ ይደረግባቸዋል፡፡ የአዜብን
አስተያየት ተከትሎ ለተቃውሞ እጃቸውን ያወጡት አርከበ እቁባይና ስዩም መስፍን ነበሩ፤ በተለይ አርከበ ‹‹ከሁለት ዓመት በፊት መለስ
እያለ ተስማምተን ያፀደቅነው እያለ ዛሬ አንቺ ይህን ሃሳብ ከየት አመጣሽው?›› ሲሉ ክፉኛ ተቃውሞአቸዋል፡፡ ምን አልባት የአዜብ ሃሳብ
ተቀባይነት ቢያገኝ ኖሮ የተጠቀሰውን መስፈርት የሚያሟሉ ብቸኛው የስራ አስፈፃሚ ሴት አባል እሳቸው በመሆናቸው ዛሬ ወይ
ጠ/ሚንስትር አሊያም ምክትል ጠ/ሚንስትር ወንበር ላይ ተቀምጠው ልናያቸው እንችል ነበር፡፡ እናም የሴቲቱን እምቢተኝነት
ከለጠጥነው ከዚህም ጋር ሊያያዝ ይችላል፡፡ ሁለተኛው አደጋ ያልኩት ደግሞ ይህ የሴቲቱ ጉልበተኝነት (ፍላጎትን በኃይል ማስፈፀም)
በቀጣይነትም በመንግስትም ሆነ በፖለቲካ ጉዳዮች ላይ ጣልቃ ላለመግባቱ ዋስትና ያለመኖሩን ነው፡፡መቼም ስለ‹‹መንግስት›› ስናወራ ስለብዙ ነገር ነው የምናወራው፡፡ መንግስት በህግ ከተደራጁት ተቋማት እና በህግ ከተፈቀደለት ስራዎች
ባሻገር አይን የማያያቸው፣ ጆሮ የማይሰማቸው ለጥቂቶች ብቻ የተፈቀዱ በርካታ ስራዎችንም የሚሰራ መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ በተለይም
በአምባገነን ስርአት ውስጥ እንዲህ አይነት ሚስጥራዊ አሰራር በስፋት ይታያል፡፡ ሲሰሙ የሚያጥውለውሉ፣ እራስን የሚያስቱ   በመንግስት
የሚፈፀሙ ምስጢሮችንም ከቶ ማን ያውቃቸዋል? ለሃያ አንድ ዓመታት በኢትዮጵያ የነበረው መንግስት በጥቂት ሰዎች ተይዞ የነበረ
በመሆኑ፣ እንዲህ አይነት ‹‹ጉዳ-ጉዶች››ን የሰማቸው የለም፡፡ ሆኖም ነገሮች ቦታ ቦታቸውን ከመያዛቸው በፊት ድንገት ከ‹‹ጥቂቶቹ››
ውጭ የነበሩት የደቡቡ ሰው የመንግስት የመጨረሻው ሰው ሆነዋል፡፡ እናም ያልተፈቀደላቸውን ሚስጥሮች ይሰሙ ዘንድ የተቀመጡበት
ወንበር ያስገድዳቸዋል፡፡ ለምሳሌም በ2003 ዓ.ም ዩናይትድ ኔሽን ‹‹ከኢትዮጵያ ተዘርፎ በውጭ ሀገር የተደበቀ›› ሲል ያጋለጠውን 8.2
ቢሊዮን ዶላር ባለቤቶች ሊያውቁ መቻላቸውን መገመት ይቻላል፡፡ መገመት የማይቻለው ካወቁ በኋላ ምን ያደርጉ ይሆን? የሚለውን
ነው፡፡ ለነገሩ ከእርሳቸው ጀርባ ያሉ ሰዎች በስራቸው ላይ ጣልቃ ይገቡ ዘንድ የሚያስገድዳቸውም እንዲህ አይነት ሚስጥሮች ተቀብረው
እንዲቀሩ ነው፡፡  በግልባጩ ደግሞ በአሁኑ ወቅት አብላጫው ኢትዮጵያዊ በሀገሪቱ ላይ መንግስት መኖሩን ማረጋገጥ እንዲፈልግ
ያስገደዱት የእዚህ አይነት ግፊቶች ናቸው፡፡ ስለዚህም ይህ ጥያቄ መልስ እስኪያገኝ ድርስ ደጋግሞ መጠየቁን ይቀጥላል ‹‹ኢትዮጵያ ሆይ
መንግስትሽ ከወዴት አለ?››
           ከ‹‹መለስ ራዕይ›› ጀርባ
የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ህይወት ማለፉን መንግስት በይፋ ከተናገረ ከሰባ ቀናት በላይ ያስቆጠረ ቢሆንም ዛሬም ድረስ
መለስ በህይወት ያሉ እስኪመስል ድረስ በሀገሪቱ እያንዳንዱ እንቅስቃሴ ላይ ስማቸው መነሳቱ የእለተ ተዕለት ተግባር ሆኖአል፡፡ በእርግጥ
ይህ የሆነው በህይወት ያሉት የአቶ መለስ ጓደኞች ከመለስ ጋር ‹‹ፍቅር እስከ መቃብር›› የሚያስብል ግንኙነት በማሳለፋቸው አይደለም፡፡
ወይም መለስ መልካም አለቃ ስለነበሩም አይደለም፡፡ የዚህ ሁሉ ዋነኛው ምክንያት መለስ በጠንካራ መዳፋቸው ሠጥ-ለጥ አድርገው
ተቆጣጥረውት የነበረውን ስልጣን ህይወታቸው ካለፈ በኋላም ‹‹በስማቸው›› እንደነበረ ለማስቀጠል ነው፡፡ ስለዚህም በመለስ ዘመን
የነበረው ኢህአዴግ በመንበሩ እስከቀጠለ ድረስ ይህ ሁኔታ አይቋረጥም፡፡ ይህ መፈክር በአመራሩ ዘንድ ፓርቲውን ከመከፋፈል የሚታደግ
ብቸኛ መጫወቻ ካርታ ሆኖ እስከመታየት ደርሷል፡፡
እስከአሁን ድርስም ኢህአዴግ ‹‹የመለስን ራዕይ›› እናሳካለን በሚል መፈክር ስር በርካታ ህዝብ እና የራሱን ካድሬ ማሰባሰብ ችሎአል፡፡
በተጨማሪም የተበታተኑና ለመፈንዳት የተቃረቡ ሕዝባዊ ቁጣዎችን ያላንዳች ኮሽታ ማምከኑም ተሳክቶለታል፡፡ ወደፊትም በመፈክሩ
ደጋፊ እያሰበሰበ፤ ተቃዋሚዎችንም እያሸማቀቀበት የመጓዝ እቅድ ይኖረዋል፡፡
ይህም ሆኖ ‹‹የመለስ ራዕይ›› ከውስጥ እንጂ ከውጭ ለሚነሳ የፖለቲካ ልዩነት መድሀኒት የመሆን አቅም የለውም፡፡ ስለዚህም በአራቱ
ድርጅቶች (ህወሓት፣ ብአዴን፣ ኦህዴድ እና ደኢህዴን) መካከል ወይም በታጠቀው ኃይል የመጠቀም ችሎታ ያለው ቡድን በኢህአዴግ
ውስጥ ልዩነት ይዞ ቢወጣ የግንባሩ እድል ፈንታ የመጨረሻው ከመሆን የሚታደገው አይኖርም፡፡ እየታየ ያለው ሁኔታም ፓርቲው በዚህ
የአንድነት መንፈስ ብዙ ሊቆይ እንደማይችል አመላካች ነው፡፡ ምንአልባትም በዚህ ወቅት ኢህአዴግ መለስ የግድ ያስፈልጉት እንደነበረ
በሀዘን እያስታወሰ ይመስለኛል፡፡ እርሳቸው ከመድረኩ የሚወርዱት የቤት ስራቸውን ሲጨርሱ ካልሆነ አደጋ መከሰቱ አይቀሬ እንደሆነም
ሁሉም ጠንቅቀው ያውቁ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ከጥቂት አመታት በፊት መለስ ወደፊት በህወሓት የበላይነት የስልጣን ወሰንን ማስከበር
እንደማይችል ተረድተው ግሩም ቲያትር ማዘጋጀት ጀምረው የነበረው፡፡
        አቶ መለስ የመውጫ እስትራቴጂ ማፈላለግ ከጀመሩ ጥቂት አመታት አልፈዋል፡፡ እናም እንደአማራጭ ይሆን ዘንድ ቲያትር መሰል
ባህሪ ያለውን ‹‹መተካካት›› አዘጋጁ፤ ከዚህ አንፃርም ነው ዛሬ እየታየ ያለው ቲያትር አዲስ ያልሆነብን፡፡ በእርግጥ ተዋንያኑ አዲስ ናቸው-
ኃይለማርያም ደሳለኝ እና ደመቀ መኮንን፡፡ አቶ መለስ ይህንን የትርጀዲ ዘውግ ያለውን ቲያትር ማዘጋጀት የጀመሩት ከድህረ ምርጫ 97
በኋላ ነው፡፡ ምክንያቱም ያንጊዜ ነው ኢትዮጵያን የምታህል ትልቅ ሀገር ሕዝቦቿን ‹‹ትምክህተኛ፣ ጠባብ፣ የደርግ ስርዓት ናፋቂ…››፤
ባንዲራዋን ደግሞ ‹‹ጨርቅ›› እያሉ ኢህአዴግን ከመሰረቱት አራቱ ፓርቲዎች ውስጥ በሚወክለው የህዝብ ቁጥር ትንሹ በሆነው ህወሓት
ስም ብዙ ርቀት መጓዝ እንደማይቻል የተገለፀላቸው፡፡ በተጨማሪም በብሔር ፖለቲካ ‹‹ሳጋና ማገር›› የቆመው ‹‹ስርዓተ መንግስት››
ውስጥ የህወሓት የበላይነት ወደፊትም በዚህ መልኩ እንደተጠበቀ መቆየቱ አጠራጣሪ ከሆነ ውሎ አድሯል፡፡ አንድ አጥኝም አቶ መለስ
በአንድ ወቅት ለህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ይህንን የሚያጠናክር ንግግር መናገራቸውን ገልጸዋል ‹‹At a meeting of the
TPLF Central Committee that was convenced at the Economic Commission for Africa hail in Addis Ababa,
the Prime Minister dropped a bombshell.He told the members who were hitherto in control of every
policy decision not only in Tigray, but also in the rest of Ethiopia that the Mandate of TPLF was over.››
(በአፍሪካ የኢኮኖሚ ኮሚሽን አዳራሽ በተካሄደው የህውሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስደንጋጭ ነገር ተናገሩ፤ እስከ
ጊዜው ድረስ በትግራይ ክልል ብቻም ሳይሆን በኢትዮጵያም በአጠቃላይ የፖሊሲ ውሳኔዎች ላይ የበላይነት ለነበራቸው የፓርቲው አባላት
የህወሓት የበላይነት ማብቃቱን ገለፁ)   የማታ ማታም አቶ መለስ ከዚህ በፊት የነበሩ ልማዶችን እና አሰራሮችን በመቀመር አስተዳደራቸውን ወደ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ
(በይዘት ሳይሆን በቅርፅ) ለማሸጋገር ቀን እና ሌሊት ይተጉ ዘንድ ግድ ሆነ፡፡ በውጤቱም ዛሬ በኃይለማርያም ደሳለኝ እና በደመቀ መኮንን
ፊት መሪነት የሚመራውን ቲያትር አዘጋጅተው መጨረሳቸው እውነት ነው፡፡ ሆኖም ቲያትሩ ለዕይታ ከመብቃቱ በፊት ህይወታቸው
በማለፉ የድርሰቱ ሰምና ወርቅ ባልገባቸው ጓዶቻቸው አዘጋጅነት ቲያትሩም ለተመልካች መቅረቡ እውነት ነው፡፡ (በነገራችን ላይ አቶ
መለስ ተፈጥሮ ባትቀድማቸው ኖሮ ትያትሩ ለአቅመ-መድረክ ይብቃ የነበረው በ2007 ዓ.ም. ከሚደረገው ምርጫ በኋላ ነበር፡፡ ያን ጊዜም
ግዙፉ የህወሓት እጅ በመድረኩ ላይ አይታይም፡፡ ከጀርባ ይሆን ዘንድ ነው የታሪኩ ሴራ የሚያጠነጥነው) መለስ ህወሓትን ይዘው ከዚህ
በኋላ በነበረው መንፈስ መጓዝ እንደማይችሉ በሚገባ መረዳታቸው ነው ለሃያ አንድ ዓመት ያህል በስልጣን ላይ ያቆያቸውን ስልት
በአዲስ ለመቀየር የተገደዱት፡፡ ይህ ሁኔታም በሁለት ተከፍሎ ለታይ ይችላል፡፡ አሮጌው (ክፍል አንድ) እና አዲሱ (ክፍል ሁለት) ተብሎ፡፡
እናም አቶ መለስ ይህን ስልት ከየት እንደቀዱት አነፃፅረን ብናቀርበው ጉዳዩን ይበልጥ ግልፅ ያደርገዋል፡፡
የ‹‹አልበርት ሴራውት›› መንገድ-ክፍል አንድ
ህወሓት ለ17 አመታት በዱር፣ በገደል ወጥቶ ወርዶ የታገለ በመሆኑ ሁሉን የመቆጣጠር ፍላጎቱን ለመግታት አልተቻለውም፡፡ ይህ
ፍላጎቱም ቤተ-መንግስቱን፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርን፣ የመከላከያ ሚኒስትርን፣ የደህንነት ሚኒስትርን፣ የሠራዊቱን ኤታማዞር ሹም፣
ባንኩን፣ ንግዱን፣ ቀረጡን… ሁሉንም ጠቅልሎ እንዲይዝ አደረገው፡፡ ሁኔታው ሁሉ ከስድስት አስርት አመታት በፊት በርካታ የአፍሪካ
ሀገራትን በቀኝ ግዛት ከያዘው የፈረንሳይ አስተዳደር የተኮረጀ መሆኑን ማየት ይቻላል፡፡ ፈረንሳይ በቅኝ ግዛት በያዘቻቸው ሀገራት ላይ
‹‹የቀጥታ አስተዳደር›› (Direct Rule) ፍልስፍናን በመተግበር ትታወቃለች፡፡ የሀሳቡ አመንጪም ‹‹አልበርት ሴራውት›› ይባላል፡፡
በዚህ የአስተዳደር ዘይቤ መርህ መሰረትም በሁሉም ቀኝ ተገዥ ሀገራት ከላይ ሆነው ስልጣን የሚይዙት ፈረንሳዊያን ብቻ መሆናቸውን
ይደነግጋል፡፡ …. ህወሓት ለሁለት አስርት አመታት የተከተለውም ይህንኑ የአልበርት ሴራውት መንገድ ነው፤ ሌላ አይደለም፡፡
የ‹‹ሎርድ ሉጋርድ›› መንገድ-ክፍል ሁለት ሌላዋ ዝነኛ ቅኝ ገዢ ሀገር ታላቋ ብሪታኒያ /እንግሊዝ/ ነበረች፡፡ እንግሊዝ በቅኝ ግዛት
በምታስተዳድራቸው ሀገራት ትከተል የነበረው የአስተዳደር ዘይቤ ከፈረንሳይ ይለያል፡፡ የእንግሊዞቹ ‹‹የዘወርዋራ አስተዳደር››
(Indirect Rule) የሚል ፍልስፍናን የሚከተል ሲሆን የሀሳቡ አመንጪም ‹‹ሎርድ ሉጋርድ›› የተባለ ሰው ነው፡፡ …አቶ መለስ
‹‹ከሚቀጥለው ምርጫ በኋላ ስልጣኔን እለቃለሁ›› ሲሉ የገቡት ቃል በሌላ አማርኛ ሲገለፅ የሎርድ ሉጋርድን መንገድ እከተላለሁ የሚል
እንደሆነ እርግጠኛ መሆን ነበረብን፡፡ ልዩነቱ መለስ የአምባገነን ስርዓት መሀንዲስ ሲሆኑ፣ ሉጋርድ የቅኝ ገዥ መሀንዲስ መሆናቸው ብቻ
ላይ ነው፡፡
እናም ሰውየው ተፈጥሮ ባትቀድማቸው ኖሮ ከመድረኩ መገለላቸው አይቀሬ መሆኑ ላይ ጥርጣሬ የለኝም፡፡ ስለዚህም ከሚቀጥለው
ምርጫ በኋላ መለስ እና ህወሓትን ከፊት መስመር አለማየታችን እውነት ነበር፡፡ ይህ የአቶ መለስ የሂሳብ ስሌት ከምርጫ 07 በኋላ እነ
ኃይለማርያምን ከፊት እንዲያስቀምጥ ተደርጎ ነው የተበጀው፡፡ ‹‹የመለስ ራዕይ›› ማለትም ይህ ነው፤ ሌላ አይደለም፡፡
አቶ መለስ አንሰላስለው የደረሱበት መደምደሚያ ከሚቀጥለው ምርጫ በኋላ ህወሓት አናሳ ቁጥር ይዞ በኢህአዴግ ውስጥ የበላይ ሆኖ
ለመቀጠል አለመቻሉን ብቻ ሳይሆን ይህንን ፍላጎቱን እንደከዚህ ቀደሙ በኃይል አስፈፅማለሁ ቢል ተግዳሮት የሚገጥመው ከተቃዋሚ
ድርጅቶች ብቻ ሳይሆን ከራሱ ከኢህአዴግ ውስጥ ጭምርም እንደሆነ ነው፡፡ ስለዚህም ይህንን አደጋ ለመከላከል ህወሓት የግድ ከመድረኩ
በሚታይ መልኩ ተገልሎ፣ በማይታይ መልኩ መቀጠል መቻል አለበት፡፡ ዛሬ የሆነውም ይህው ነው፡፡ በእርግጥ ይህ የፖለቲካ ጨዋታ
አደባባይ የወጣው ‹‹መተካካት›› በሚል የዳቦ ስም ነው፡፡ ምናልባትም አዜብ መስፍን ከሳምንታት በፊት ለአንድ በትግሪኛ
ቋንቋ ለሚዘጋጅ ሚዲያ በሰጡት ቃለ መጠይቅ ላይ ‹‹የትግራይ ህዝብ፣ የህወሓት መንፈስና የመለስ ራዕይ እስካሉ ድረስ ሁሉንም
እንወጣዋለን›› ያሉት ከዚህ ተነስተው ሊሆን ይችላል፡፡ (የሴቲቱ ንግግር እንደተለመደው ፕሮፓጋንዳ ‹‹የኢትዮጵያ ህዝብ፣ የኢህአዴግ
መንፈስ እና የአመራር አባላት እስካሉ ድረስ ሁሉንም ነገር እንወጣዋለን›› የሚል ቢሆን ኖሮ ሀሳባቸውን ለመተርጎም ወይም ለመተንተን
ቀዳዳ አይኖርም ነበር) የሆነ ሆኖ መለስ በህይወት ቢኖሩ ኖሮ ኢህአዴግ ያለስጋት በሂሳቡ ስሌት መሰረት በስልጣን መቀጠሉ ላይሳነው
ይችል ነበር፡፡ ሆኖም አቶ መለስ ያለጊዜው አልፈዋል፡፡ ተከታዮቻቸውም አብረዋቸው ያላዩትን ‹‹ራዕይ-መለስ›› እንደሚያስፈፅሙ
እየፎከሩ ነው፡፡ የሚቻላቸው ግን አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም እነ ኃይለማርያምን ከፊት በማድረግ ስርዓቱን ማስቀጠል የሚቻለው መለስ
በህይወት ሲኖሩ ብቻ ነው፡፡ አሁን መለስ የሉም፡፡ ተተኪዎቻቸው ደግሞ ቀመሩን በሚገባ መጠቀም የቻሉ አይመስሉም፡፡ ወይም ለእነ
ኃይለማርያም እውነተኛ ስልጣን መስጠት ይኖርባቸዋል፡፡ ነገር ግን ሶስቱም የሚቻላቸው አልሆነም፡፡ እናም ገና ከጅምሩም አንዳንድ
ክፍተቶችን እያየን ነው፡፡ ለምሳሌም ለውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ሚንስትር የሚሆነውን ሰው ከየትኛው የግንባሩ አባል ፓርቲ መመረጥ
እንዳለባቸው መወሰኑ ቸግሯቸዋል፤ ሌላው ቀርቶ የፖለቲካ አቅም የሌለውን የፕሬዘዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስን ወንበር መተካት ከነበረበት
ጊዜው አልፏል፡፡ እነዚህ ሁኔታዎች ናቸው ኢህአዴግ ወደ ማይቀረው የመከፋፈል እጣ ፈንታው እየተገፉ ያለ ያስመስሉት፡፡
‹‹ናዳን የገታ እሩጫ››
በረከት ስምዖን ባለፈው ዓመት ለአሳተሙት መፅሀፍ ግልገል ርዕስ ያደረጉት ‹‹ናዳን የገታ ሩጫ›› ይላል፡፡ እርሳቸው በዚህ ርዕስ ውስጥ
ሊያስተላልፉ የፈለጉት ጉዳይ ፓርቲያቸው ‹‹በምርጫ 97 በሕዝብ ድምፅ ከስልጣን ሊባረር አፋፍ ደርሶ ከተመለሰ በኋላ ከፍተኛ የልማትተግባራትን በመፈፀሙ ብዙሀኑን ኢትዮጵያዊ መማረክ ቻለ›› የሚል ፕሮፓጋንዳ ነው፡፡ በእርግጥ የድሉ ቁልፍ ሰው ሟቹ ጠቅላይ
ሚንስትር መሆናቸውን መፃሀፉ አልሸሸገም፡፡ ጥያቄው ግን ከዚህኛው የናዳ ዘመንስ ድርጅቱን ማን ይታደገዋል? የሚል ነው፡፡ ኢህአዴግ
ይህንን ጥያቄ በሚገባ መመለስ ከቻለ ምናልባትም ዳግም ተጠናክሮ የሚወጣበት ዕድል ሊኖረው ይችላል፡፡ ወይም አቶ መለስ ለክፉ ቀን
ያቆዩት ‹‹ፓኬጅ››ን ከእነአጠቃቀሙ ማግኘት ከቻለ ‹‹ዕድሜ ማራዘሚያውን›› አገኘ ማለት ነው፡፡ በእርግጥ ይህንንም ማድረግ ችሎ
በሀገሪቱ፣ በአባሎቹ እና በቅቡልነቱ ላይ ምን አይነት መአት ሊያስከትል እንደሚችል አስቀድሞ ማወቅ አይቻልም፡፡

No comments:

Post a Comment